የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ ውድድር ተራዘመ

የሴቶች ፕሪምየር ሊግ የሁለተኛው ዙር ውድድር የሚጀመርበት ቀን ተገፍቷል፡፡

የ2014 የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ የመጀመሪያው ዙር ጨዋታዎች በሀዋሳ ጅምራቸውን አድርገው በባህርዳር መጠናቀቃቸው ይታወሳል፡፡ የሁለተኛውን ዙር ውድድር ደግሞ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽን ከግንቦት 16 ጀምሮ በአዳማ አበበ ቢቂላ ስታዲየም ለማድረግ ቀን ቆርጦ ነበር።

ሆኖም የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ የመጨረሻ የደርሶ መልስ ጨዋታውን ከናይጄሪያ ጋር የሚያከናውን በመሆኑ እና እንዲሁም ደግሞ የሴካፋ ሴቶች ዋንጫ በዩጋንዳ ሲደረግ ሀገራችን ኢትዮጵያ ተሳታፊ በመሆኗ ቀኑ ማሻሻያ ተደርጎበታል።

ሁኔታውን ከግንዛቤ በማስገባት በዛሬው ዕለት የፌዴሬሽኑ የበላይ አካላት ከክለብ አመራሮች ጋር ባደረጉት ውይይት መግባባት ላይ በመደረሱ ውድድሮች የሚገባደዱበትን ቀን ታሳቢ ባደረገ መልኩ ፕሪምየር ሊጉ ሰኔ 11 እንዲጀመር በማለት ከስምምነት ደርሰዋል፡፡

አንዳንድ ክለቦች የተጫዋቾች ኮንትራት የሚጠናቀቀው ሰኔ 30 በመሆኑ እንዴት ሊሆን ነው በማለት ሀሳብ ያነሱ ቢሆንም ፌድሬሽኑ የውል ጊዜውም ቢያልፍ ሀገራዊ ጉዳይ ከመሆኑ አንፃር እና የተቀመጠ ደንብ በመኖሩ ተጫዋቾች ከውላቸው ውጪ ክለባቸውን እንዲያገለግሉ በማለት ተጨማሪ ውሳኔ አሳልፏል፡፡