የዋልያዎቹ እና ፈረኦኖቹን ጨዋታ የሚመሩ ዳኞች ታውቀዋል


ነገ ምሽት በኢትዮጵያ እና ግብፅ መካከል የሚደረገውን ተጠባቂ ጨዋታ የሚመሩ አልቢትሮች ታውቀዋል።

የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣሪያ ጨዋታዎች ነገም ሲቀጥሉ በምድብ አራት ከማላዊ እና ጊኒ ጋር የተደለደሉት ኢትዮጵያ እና ግብፅ የእርስ በርስ ፍልሚያቸውን በማላዊ ርዕሰ መዲና ሊሎንግዌ በሚገኘው ቢንጉ ስታዲየም ያከናውናሉ። ሁለቱም ቡድኖች ለጨዋታው በጥሩ ሁኔታ እየተዘጋጁ እንደሆነም ከስፍራው የሚወጡ መረጃዎች ያመላክታሉ።

የሁለቱን ሀገራት ተጠባቂ ጨዋታ ከዋና እስከ አራተኛ ዳኝነት እንዲመሩ የተመረጡት አልቢትሮች ደግሞ ቡሩንዲያዊ እንደሆኑ ሶከር ኢትዮጵያ አረጋግጣለች። ምሽት 1 ሰዓት ላይ የሚጀምረውን ጨዋታ በመሐል አልቢትርነት ጆርጅ ጋቶጋቶ ከመስመር ረዳቶቻቸው ኸርቨ ካኩንዜ እና ዊሊ ሀቢማና እንዲሁም አራተኛ ዳኛው ጃፋሪ ንዱዊማና ጋር በመሆን እንደሚመሩት ሲጠበቅ ሊቢያዊው ጋማል ሰላም ኢምባያ ደግሞ ኮሚሽነር እንደሆኑ ተመላክቷል።