የአሰልጣኞች አስተያየት | መከላከያ 0-0 አዳማ ከተማ

የሳምንቱ ማሳረጊያ ጨዋታ ያለ ጎል ከተጠናቀቀ በኋላ አሰልጣኞች ድህረ ጨዋታ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ – መከላከያ

ስለ ጨዋታው…?

“በመጀመሪያው አርባ አምስት ደቂቃ እኛ የተሻልን ነበርን ግን ቢኒያም ከወጣ በኋላ እስራኤል ከወጣ በኋላ ሁለት አጥቂዎች ሲወጡብን ወሳኝ አጥቂዎች ስለሌሉን ያለንን አስጠብቀን መውጣት እንዳለብን ነው ያደረግነው፡፡ የመጀመሪያው አርባ አምስት ደቂቃ ላይ ግን ሙሉ ሀሳባችን ሙሉ ሦስት ነጥብ አለን በሚል ተጭነን ነው የተጫወትነው ግን ከሀያ ደቂቃዎች በኋላ አጥቂዎቻችን እየወጡ ሲመጡ ያለንን አቅም ስለምናውቅ ፣ ያሉንን ተጫዋቾች ስለምናውቅ አንደኛው ፕላናችን ካልሰራ ሁለተኛውን ፕላን ይዘን መምጣት አለብን ፤ አቅምን ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ያለችውን አንዷን አስጠብቀን ለመውጣት የመጨረሻውን አስራ አምስት ደቂቃ በርትተናል፡፡

ያለፉትን ሦስት ጨዋታዎች ቡድኑ ጎል ያለ ማስቆጠሩ ከአጥቂ ጥራት አንፃር …?

“ይሄ የሀገሪቱ ችግር ነው፡፡ አጥቂ ደግሞ እንዲህ በቀላሉ የሚገኝ አይደለም፡፡ ብዙ ሥራ የሚጠይቅ ነው ፤ አቅም ይጠይቃል፡፡ በዛች በሰባት ሜትር ምናምን ውስጥ ጎል ለማስገባት አቅም ይጠይቃል፡፡ ከአቅም ጋር ከፍተኛ የሆነ የሥነ ልቦና ይፈልጋል። የእኛ ተጫዋቾች ከዕረፍት በፊት መአት ኳስ ነው ያገኙት ጠንካራ እግሩ በቀኝ ሆኖ በግራ እግሩ ይመታል፡፡ አሁን ይሄ የሥነ ልቦና ጉዳይ ነው፡፡ ኳሱን ይዘኸው በጠንካራው እግር መምታት አምስት ኳስ የቀኝ እግር አምስት ተጫዋቾቻችን በግራ መተዋል፡፡ ይሄ ምንድነው የሚያሳየህ የጨዋታ ጉጉት ትልቅ የሥነ ልቦና ሥራ ይጠይቃል፡፡ ሰውን በአንድ ዓመት በአንድ ጊዜ የምትሰራው አይደለም፡፡ በትልልቆቹ ሊጎች ስድስት ወር ፣ ሰባት ወር የማያገቡ አሉ የእኛን ደግሞ ትቀበላህ፡፡”

አሰልጣኝ ይታገሱ እንዳለ – አዳማ ከተማ

አንድ ነጥብ ብቻ ስለማግኘታቸው…?

“አጥጋቢ አይደለም፡፡ የምታገኘውን ነገር መቀበል ነው፡፡ በይበልጥ አጥቅተን ለመጫወት ነበር የሞከርነው እንደሚታየው ነው፡፡ ሦስት ነጥብ ፈልገን ነበር የገባነው አልተሳካም፡፡

ከባለፈው አሰላለፍ ወሰኑ ዓሊን በአቡበከር ወንድሙ ለውጠው መጠቀማቸው…?

“መጀመሪያ አርባ አምስት ላይ ወሰኑ የተሻለ ልምድም አለው፡፡ ከዚህ በፊት የምንቸገርበት የነበረው ትንሽ መረጋጋት ነበር። ማጥቃት ላይ ወሰኑ ትንሽ ልምድም ስላለው ረጋ ብሎ ይጫወታል ብዬ ስላሰብኩኝ ለውጡን እንደፈለኩት አግኝቼዋለሁ፡፡ ጎል ካለማስቆጠር ውጪ፡፡

ስለ ቀጣይ ሁለት ወሳኝ ጨዋታዎች…?

“የደረጃ ሰንጠረዣችን በጣም ተቀራራቢ ነው፡፡ ሁለቱ ጨዋታዎች በራሳችን ነው የምንወስነው፡፡ የሰው ዕድል አይደለም የምናየው በራሳችን እጅ ስለሆነ እናሳካዋለን ብዬ አስባለሁ፡፡

በአንተ ዕይታ በሊጉ አዳማ አይወርድም…?

“መቶ ፐርሰንት አይወርድም፡፡ የተሻለ ነገር ይኖራል በራሳችን እጅ ነው፡፡ ማንም ወርዶ መጫወት የሚፈልግ የለም ፣ ከተጫዋቾቹ ጀምሮ እኔንም ጨምሮ ትልቅ ቡድን ነው የያዝነው። ልምዳችንን ተጠቅመን ያለውን እናደርጋለን፡፡ ሁለቱን ጨዋታዎች የተሻለ ነገር አሳይተን በሊጉ ላይ እንቆያለን፡፡”