የአሰልጣኞች አስተያየት | ሰበታ ከተማ 1-0 አርባምንጭ ከተማ

ሊጉን የተሰናበተው ሰበታ ከተማ በመጨረሻ ጨዋታው ሦስት ነጥብን ከአርባምንጭ ከተማ ከወሰደበት ፍፃሜ በኋላ አሰልጣኞች አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

አሰልጣኝ ብርሀን ደበሌ – ሰበታ ከተማ

ስለ መጨረሻ የፕሪምየር ሊግ ጨዋታቸው

“በክብር ተሸኝተናል ማለት ይቻላል፡ ፤ ይሄን የመጨረሻ ድላችንን አሸንፈናል። ሆኖም ግን ቅር እያለን ብንወርድም ተግተን ደግሞ ሰርተን ፣ ያለፉት ስህተቶች ታርሞ እግርኳሳዊ በሆነ እንቅስቃሴ ውስጥ ገብተን ጥሩ ቡድን ሰርተን ወደ ላይ የምንመጣበት ጊዜ ሩቅ አይመስለኝም፡፡

በጨዋታው ስለተደረጉ ቅያሪዎች

“መጀመሪያ እነዚህን ተጫዋቾች የተጠቀምነው ፣ ትንሽ አቅማቸውን አይተን በእነርሱ ላይ መለወጥ ስላለብን እንጂ መጀመሪያ ቀድመን አስገብተን መለወጡ አጥጋቢ እንደማይሆን ስላወቅን እነዚህን ተጫዋቾች ወደ በኋላ አስገብተናቸዋል፡፡

ስለ ወጣቱ ግብጠባቂ ቶማስ ትዕግስቱ

“ቶማስ በጣም ግሩም እና ድንቅ የሆነ ተጫዋች ነው፡፡ ዓለማችን አሁን በእግርኳስ ውስጥ በእግር መጫወት ትልቁን ቦታ ይሰጣል፡፡ ስለዚህ አንብቦም የሚጫወት ነው፡፡ የልጅ አዋቂ ነው ማለት ይቻላል። በይበልጥ እየጠነከረ ከሄደ ፣ የተሻለ ነገር ያሳያል ወደ ፊትም ትልቅ ተስፋ ያለው ነው ፤ እተማመንበታለሁ።”

አሰልጣኝ መሳይ ተፈሪ – አርባምንጭ ከተማ

ስለ ጨዋታው

“በመጀመሪያው ጨዋታውን ተቆጣጥረን ተጫውተናል፡፡ ግን ሳጥን ውስጥ ስንገባ ቁጥራችን አነስተኛ ነው፡፡ በምንፈልገው ልክ አይደለም የጎል አጋጣሚዎችን ስንፈጥር የነበረው፡፡ ወደ መጨረሻዎቹ አካባቢ ጎል ከተቆጠረብን በኋላ ቶሎ ቶሎ ለማግባት ጥረት አድርገናል አልተሳካም፡፡

የእንዳልካቸው እና አህመድ ከወትሮው መቀዛቀዝ

“የሚሄዱ ኳሶች ምናልባት የመሀል ተከላካይ ቀድሞ ስፔሱን ይይዝ ነበር፡፡ የሚመቱ ኳሶችን ተቆጣጥሮ ነበር ይመጣ የነበረው ፤ ሌሎች አማራጮች ነበሩ አንዳንዴ አይሳካም፡፡

ስለነበረው የአጨራረስ ድክመት

“በተወሰነ መልኩ ኳሶችን ተቆጣጥረን ስንጫወት ትዕግስት ይፈልጋል፡፡ ከሌላው ጊዜ በተለየ ጥሩ እንቅስቃሴ ነበር በመጀመሪያው አጋማሽ ላይ ግን ይሄ ብቻ በቂ አይደለም፡፡ መጨረሻ ላይ የምናገኛቸውን የቆሙ ኳሶች እና ወደ ጎል የምንደርሳቸውን ላይ ማስቆጠሩ ላይ መጨመር አለብን፡፡ ሆኖም ጠንካራ ነገሮችን አይቻለሁ ወጣት ተጫዋቾች ጥሩ ነገርም ሲሰሩ አይቻለሁ፡፡

ስለቀጣዩ የ2015 የውድድር ዘመን

“ዘንድሮ ከነበረው የተሻለ ነገር ይዘን እንቀርባለን፡፡ ዘንድሮ ካሳየነው ደግሞ ከፍ አድርገን አሻሽለን እንመጣለን፡፡”