ሲዳማ ቡና ተጫዋቾቹን እና አሰልጣኞቹን ሸልሟል

ፕሪምየር ሊጉን ሦስተኛ በመሆን ያጠናቀቀው ሲዳማ ቡና ለቡድን አባላቱ የማበረታቻ ሽልማት ሲሰጥ አጥቂው ይገዙም ተመስግኗል።

የ2014 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግን በአሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ ጀምሮ በረዳቱ ወንድማገኝ ተሾመ የጨረሰው ሲዳማ ቡና ሊጉን ከቅዱስ ጊዮርጊስ እና ፋሲል ከነማ በመቀጠል ሦስተኛ ደረጃን ይዞ ካጠናቀቀ በኋላ በዛሬው ዕለት በሀዋሳ ኃይሌ ሪዞርት የክለቡ ምክትል ፕሬዝዳንት እና የሲዳማ ክልል የባህል እና ስፖርት ቱሪዝም ቢሮ ሀላፊ አቶ ጃጎ አገኘሁ እንዲሁም የክለቡ የበላይ አካላት እና የቦርድ አመራሮች በተገኙበት ለተጫዋቾቹ እና አሰልጣኞቹ የማበረታቻ ሽልማትን ተበርክቷል፡፡

ክለቡ ለቡድኑ አጠቃላይ አባላት የ5 ሚሊዮን ብር ሽልማት ሲያበረክት የቡድኑ አጥቂ ለሆነው እና ዓመቱን የሊጉ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ (በ16 ጎሎች) ሆኖ ላጠናቀቀው ይገዙ ቦጋለ ተጨማሪ የ100 ሺ ብር ሽልማትን መሰጠቱን ክለቡ ለሶከር ኢትዮጵያ የላከው መረጃ ይጠቁማል፡፡