ወጣቱ አጥቂ ለቡናማዎቹ ለመጫወት ተስማምቷል

በዝውውር ገበያው በንቃት እየተሳተፉ የሚገኙት ኢትዮጵያ ቡናዎች ወጣቱን አጥቂ ለማስፈረም ስምምነት ላይ ደርሰዋል።

ኢትዮጵያ ቡና ኃይለሚካኤል አደፍርስ እና አብዱልአዚዝ ቶፊቅን በይፋ ማስፈረሙ ሲረጋገጥ አብዱልከሪም ወርቁን ደግሞ ዛሬ በይፋ ወደ ስብስቡ መቀላቀሉን እንደሚያስተዋውቅ ይጠበቃል። አሁን ባገኘነው መረጃ ደግሞ ፈጣኑን አጥቂ መስፍን ታፈሰን ለማስፈረም ከተጫዋቹ ጋር መስማማታቸውን አውቀናል።

ከሀዋሳ ታዳጊ ቡድን አንስቶ እስከ ዋናው ቡድን ድረስ በመጫወት የሚታወቀው መስፍን ያለፉት ሁለት ዓመታት በሊጉ በድንቅ አጥቂነታቸው ራሳቸውን ማሳየት ከቻሉ አጥቂዎች ተርታ የሚመደብ ሲሆን ለኢትዮጵያ ቡናም የተሻለ ግልጋሎት ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።

አምስት ተጫዋቾችን ብቻ በቡድኑ ውስጥ እንደሚያቆይ የተሰማው ኢትዮጵያ ቡና ዛሬ እና ነገ ሌሎች ተጨማሪ ተጫዋቾችን ወደ ቡድኑ እንደሚቀላቅል ይጠበቃል።