ሀዋሳ ከተማ ሁለት ተጨማሪ ተጫዋቾችን አስፈርሟል

የወሳኝ ተጫዋቹን ሙጂብ ቃሲም ዝውውር ከደቂቃዎች በፊት የፈፀመው ሀዋሳ ከተማ ተጨማሪ ሁለት ተጫዋቾችን ወደ ቡድኑ ቀላቅሏል፡፡

በትላንትናው ዕለት ወደ ዝውውሩ ጎራ በማለት በረከት ሳሙኤል እና እዮብ አለማየሁን ያስፈረመው እና ከደቂቃዎች በፊት ደግሞ ሙጂብ ቃሲምንም የቀላቀለው ሀዋሳ ከተማ አመሻሹን ሁለት ተጫዋቾችን በመጨመር የአዳዲስ ፈራሚዎቹን ቁጥር አምስት አድርሷል፡፡

ሰዒድ ሀሰን አራተኛ የክለቡ ፈራሚ ሆኗል፡፡ በፋሲል ከነማ ቤት ከከፍተኛ ሊግ ጀምሮ እስከ ተጠናቀቀው የውድድር ዓመት ድረስ በክለቡ ያሳለፈው የቀኝ መስመር ተከላካዩ መዳረሻው በሁለት ዓመት ውል ሀዋሳ ሆኗል፡፡


ሌላኛው ፈራሚ አዲሱ አቱላ ነው፡፡ ከሲዳማ ቡና ወጣት ቡድን ከተገኘ በኋላ ለዋናው ቡድን አራት ዓመታትን ግልጋሎት የሰጠው ይህ የመስመር አጥቂ በዘንድሮው የውድድር ዓመት በመከላከያ ጥሩ ጊዜን ያሳለፈ ሲሆን በሲዳማ ቡና ካሰለጠነው አሰልጣኝ ዘርአይ ሙሉ ጋር ዳግም የተገናኘበትን ዝውውር አጠናቋል፡፡