አፄዎቹ የሁለት ተጫዋቾችን ውል አራዘሙ

ፋሲል ከነማ ትናንት እና ዛሬ እንዳደረገው ሁሉ አሁንም ከነባር ተጫዋቾቹ መካከል ከሁለቱ ጋር አብሮ ለመቀጠል ወስኗል።

ከአዳዲስ ዝውውሮች ይልቅ የነባር ተጫዋቾቹን ውል በማራዘም የተጠመደው ፋሲል ከነማ ከሽመክት ጉግሳ ፣ በዛብህ መለዩ እና ሱራፌል ዳኛቸው በመቀጠል የይሁን እንዳሻው እና ፍቃዱ ዓለሙን ኮንትራት አራዝሟል፡፡

ለመከላከያ ለመጫወት ቀትር ላይ ተስማምቶ የነበረው ይሁን እንዳሻው የፋሲል ከነማን ጥሪ በመቀበል ዳግም በክለቡ መቆየትን መርጧል፡፡ የቀድሞው የድሬዳዋ ከተማ ፣ ጅማ አባ ጅፋር እና ሀድያ ሆሳዕና የአማካይ ስፍራ ተጫዋች ሁለት ዓመታትን በፋሲል ከነማ ቤት ጥሩ ቆይታ የነበረው ሲሆን ለቀጣዮቹ ተጨማሪ ዓመታትም በክለቡ ለመቆየት ከሰዓታት በፊት ፊርማውን አኑሯል፡፡

አጥቂው ፍቃዱ ዓለሙ አምስተኛ ውል ያደሰ የፋሲል ተጨዋች ሆኗል፡፡ የቀድሞው የአዲስ አበባ ከተማ እና መከላከያ አጥቂ ያለፉትን ሁለት ዓመታት በፋሲል ያሳለፈ ሲሆን ተጨማሪ ሁለት የውድድር ዘመናትን ለማሳለፍም ውሉን ከደቂቃዎች በፊት አድሷል፡፡