ሀድያ ሆሳዕና የሁለት ተጫዋቾችን ውል አራዝሟል

ከሰሞኑ የአዳዲስ ተጫዋቾችን ዝውውር በመከወን እና የነባሮችን ኮንትራት በማደስ ላይ የሚገኙት ሀድያ ሆሳዕናዎች የሁለት ተጨማሪ ነባር ተጫዋቾችን ውል አድሰዋል፡፡

በቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የሁለተኛ ዓመት ተከታታይ ተሳትፎውን ለማድረግ የሦስት አዳዲስ ተጫዋቾችን ዝውውር የፈፀመው እና የሦስት ነባር ተጫዋቾችን ኮንትራት ያደሰው ሀድያ ሆሳዕና በዛሬው ዕለት የሁለት ተጨማሪ ነባር ተጫዋቾችን ውል ለአንድ ተጨማሪ ዓመት አራዝሟል።

ውላቸው ከተራዘመላቸው ተጫዋቾች አንዱ ባዬ ገዛኸኝ ነው፡፡ የቀድሞው የወላይታ ድቻ ፣ መከላከያ እና ሲዳማ ቡና የአጥቂ ስፍራ ተጫዋች የሆነው ባዬ የተጠናቀቀውን የውድድር ዘመን ባሳለፈበት ሀድያ ሆሳዕና ተጨማሪ አንድ ዓመትን ለመቆየት ውሉን አድሷል፡፡

ሳምሶን ጥላሁንም ሌላኛው በክለቡ ውሉን ያራዘመው ተጫዋች ሆኗል፡፡ በቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ ኢትዮጵያ ቡና ፣ ደደቢት እና ባህር ዳር ከተማ በመጫወት ከዚህ በፊት የሚታወቀው የአማካይ ስፍራ ተጫዋቹ የ2014 የውድድር ዘመንን በነብሮቹ ቆይታ የነበረው ሲሆን ዳግም ሁለተኛ ዓመቱን በክለቡ መለያ ለመታየት ውሉ ታድሶለታል፡፡