ኢትዮ ኤሌክትሪክ የምንያህል ተሾመን ውል አድሷል

ፕሪምየር ሊጉን ዳግም የተቀላቀለው ኢትዮ ኤሌክትሪክ የአማካዩን ቆይታ ለተጨማሪ አንድ ዓመት አራዝሟል።

የአሠልጣኝ ክፍሌ ቦልተናን ውል ካደሰ በኋላ ፊቱን ወደ ተጫዋቾች የዝውውር መስኮት ያዞረው ኢትዮ ኤሌክትሪክ አዳዲስ ተጫዋቾችን ከማስፈረሙ ጎን ለጎን የነባር ተጫዋቾችንም ውል እያደሰ ይገኛል። ከደቂቃዎች በፊትም የአንጋፋውን አማካይ ምንያህል ተሾመን ውል ለተጨማሪ አንድ ዓመት ማደሱን ሶከር ኢትዮጵያ አረጋግጣለች።

የቀድሞው የኢትዮጵያ ቡና፣ ደደቢት፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ወልድያ እና ድሬዳዋ ከተማ የመሀል ሜዳ ተጫዋች ምንያህል ዘለግ ላለ ጊዜ ከሜዳ ከራቀ በኋላ በተጠናቀቀው የውድድር ዓመት በከፍተኛ ሊግ ምድብ ሀ ተወዳዳሪ ለነበረው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ፈርሞ ግልጋሎት ሲሰጥ ነበር። ክለቡን ወደ ፕሪምየር ሊግ ካሳደጉ ወሳኝ ተጫዋቾች መካከል አንዱ የሆነው የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አማካይ ዳግም በሊጉ ለመጫወት ፊርማውን ለኤሌክትሪክ አኑሯል።