ባህር ዳር ከተማ የአምበሉን ውል አድሷል

እስካሁን ስምንት አዳዲስ ተጫዋቾችን ያስፈረሙት ባህር ዳር ከተማዎች የአማካያቸውን ውል ለተጨማሪ ሁለት ዓመት አድሰዋል።

በአሠልጣኝ አብርሃም መብራቱ የሚመራው ባህር ዳር ከተማ በተጠናቀቀው የውድድር ዓመት ሳይጠበቅ በደረጃ ሰንጠረዡ የታችኛው ክፍል ረዘም ያለውን የጨዋታ ሳምንት ያሳለፈ ሲሆን በቀጣይ ዓመት ግን ተጠናክሮ ለመቅረብ አዳዲስ ተጫዋቾችን ወደ ስብስቡ እየቀላቀለ ይገኛል። ከደቂቃዎች በፊት ደግሞ የአምበሉ ፍቅረሚካኤል ዓለሙን ውል ማደሱን ይፋ አድርጓል።

የቀድሞ የፋሲል ከነማ እና አውስኮድ ተጫዋች የነበረው ፍቅረሚካኤል 2010 ላይ የጣና ሞገዶቹን ከተቀላቀለ በኋላ ያለፉትን ዓመታት ከፍተኛ አገልግሎት ሲሰጥ ነበር። ባህር ዳር ወደ ሊጉ እንዲያድግ ካስቻሉ ቁልፍ ተጫዋቾች መካከል አንዱ የሆነው አምበል ለተጨማሪ ሁለት ዓመታት በትውልድ ከተማ ለመቆየትም ፊርማውን አኑሯል።