ኢትዮጵያ ቡና የውጪ ሀገር ዜጋ አስፈረመ

ጋናዊው የመሀል ተከላካይ ኢትዮጵያ ቡናን በሁለት ዓመት ውል ተቀላቀለ።

በአሰልጣኝ ተመስገን ዳና መሪነት በርካታ አዳዲስ እና ነባር ተጫዋቾችን ይዞ ማረፊያውን በሀዋሳ ሴንትራል ሆቴል በማድረግ በግብርና ኮሌጅ ሜዳ ላይ በቀን ሁለት ጊዜ ልምምድ እየከወነ የሚገኘው ኢትዮጵያ ቡና ከዓመታት ቆይታ በኋላ ፊቱን ወደ ውጪ ሀገር በማዞር ጋናዊ የመሀል ተከላካይ በዛሬው ዕለት በይፋ በሁለት ዓመት የውል ኮንትራት የግሉ አድርጓል፡፡

አዲሱ የቡናማዎቹ የውጪ ዜጋ ፈራሚ ኩዋኩ ዱሀ ነው፡፡ 1 ሜትር ከ80 ሴንቲ ሜትር እንደሚረዝም የተነገረለት የ24 ዓመቱ የመሀል ተከላካይ የእግርኳስ ህይወቱን በሙሉ በሀገሩ ጋና ክለቦች ጎልድ ስታር ፣ ኒው ኢዱቫይስ ዩናይትድ ፣ ኪንግ ፋይሰል እና ያለፉትን ሦስት ዓመታት ደግሞ ቢቢያኒ ጎልድ ስታር በተባለ ክለብ ሲጫወት ቆይቶ ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ በመምጣት ደግሞ ቡናማዎቹን በይፋ ተቀላቅሏል፡፡

ኢትዮጵያ ቡና በያዝነው ሳምንት አንድ የውጪ ሀገር ግብ ጠባቂ ለመቀላቀል በሂደት ላይ መሆኑንም ጭምር ሰምተናል፡፡