ወላይታ ድቻ ጋናዊ አጥቂ ወደ ስብስቡ ቀላቅሏል

ጋናዊው አጥቂ ሚኬል ሳርፖንግ ወላይታ ድቻን በአንድ ዓመት ውል ተቀላቅሏል፡፡

የአሰልጣኝ ፀጋዬ ኪዳነማርያምን ውል ካራዘመ በኋላ የአዳዲስ ተጫዋቾች ዝውውር በመፈፀም እና ውላቸው ተገባዶ የነበሩ ነባር ተጫዋቾችን ኮንትራት በማራዘም በክለቡ መቀመጫ ከተማ ሶዶ የቅድመ ውድድር ዝግጅቱን እየከወነ የሚገኘው ወላይታ ድቻ ጋናዊውን የ26 ዓመት አጥቂ ሚኬል ሳርፖንግን በአንድ ዓመት ውል ወደ ስብስቡ መቀላቀሉን ክለቡ ለሶከር ኢትዮጵያ አሳውቋል፡፡

እግር ኳስን በሀገሩ ጋና ክለቦች ሊቨርቲ ፕሮፌሽናል እና ድሪምስ ኤፍ ሲ በመጫወት የጀመረው አጥቂው በመቀጠል ለሩዋንዳው ራዩን ስፖርት፣ ለታንዛኒያው ያንግ አፍሪካ እንዲሁም ያለፈውን አንድ ዓመት ደግሞ በሳውዲ አረቢያው ክለብ አል-ናህዳህ በመጫወት ቆይታን አድርጎ ዳግም ወደ ሩዋንዳ በማምራት ኤ ኤስ ኪጋሊን ከተቀላቀለ በኋላ ኢትዮጵያ በመምጣት የጦና ንቦቹን አባል ሆኗል።