ፋሲል ከነማ የመስመር አጥቂ አስፈርሟል

በትናንትናው ዕለት የግብ ዘብ ወደ ስብስባቸው ቀላቅለው የነበሩት ፋሲል ከነማዎች ዛሬ ደግሞ የመስመር አጥቂ አስፈርመዋል፡፡

በካፍ ኮንፌድሬሽን ዋንጫ በነገው ዕለት ኢትዮጵያን በመወከል ከቡሩንዲው ቡማሙር ጋር ጨዋታቸውን በባህርዳር ስታዲየም የሚያደርጉት ፋሲል ከነማዎች በትላንትናው ዕለት ከዚህ ቀደም የክለቡ ታዳጊ ቡድን ተጫውቶ ያሳለፈውንና የተጠናቀቀውን የውድድር ዓመት በከፍተኛ ሊጉ ክለብ ፌዴራል ፓሊስ ያሳለፈውን ግብ ጠባቂ ዮሐንስ ድረስን ያስፈረሙ ሲሆን በዛሬው ዕለት ደግሞ የመስመር አጥቂው ኪሩቤል ደሳለኝን የግላቸው አድርገዋል፡፡

ክለቡ እንደገለፀው ከሆነ ተጫዋቹ በአሜሪካን ሀገር በዩኒቨርሲቲ ውድድር ላይ በተለያዩ የማጥቃት ሚና ተጫውቶ ያሳለፈ ሲሆን በዐፄዎቹ ቤት የሙከራ ዕድል ተሰጥቶት በአግባቡ መጠቀም በመቻሉ በአንድ ዓመት ውል በዛሬው ዕለት ፊርማውን አኑሯል፡፡