“ጠንካራ ፉክክር እንደሚጠብቀን እናምናለን ፤ ለዚህም አዕምሯችንን ዝግጁ ማድረግ ይገባናል”- ቪቪ ባሃቲ

በነገው ዕለት በባህር ዳር ስታዲየም ፋሲል ከነማን የሚገጥመው የብሩንዲው ክለብ ቡማሙሩ አሰልጣኝ ቪቪ ባሃቲ በጨዋታው ዋዜማ ተከታዩን አስተያየት ለሶከር ኢትዮጵያ ሰጥተዋል።

ለጨዋታው ስላደረጉት ዝግጅት…?

“ዝግጅታችን ጥሩ ነበር። በቂ ጊዜ ወስደን ተዘጋጅተናል ፤ ወደ ቀጣዩ ዙር ለመሻገር ይህ ጨዋታ ወሳኝ በመሆኑ ጥሩ ዝግጅት አድርገናል።”

ስለተጋጣሚያቸው ያላቸው መረጃ…?

“በ2019 ፋሲልን የገጠመው የአዛም ቡድን አካል ነበርኩ። ምንም እንኳን ባለፉት ሦስት ዓመታት ቡድኑ በተወሰነ መልኩ የተለወጠ ቢሆንም አሁን ላይ ያላቸው ስብስብ ነገሮችን በተሻለ መንገድ መከወን የሚችል ነው። በመሆኑም ይህን ታሳቢ አድርገን ጥሩ ጨዋታ ለማሳየት እንሞክራለን።”

ስለ ተጫዋቾች ወቅታዊ ጤንነት…?

“ተጫዋቾች ሙሉ በሙሉ በጥሩ ጤንነት ላይ ይገኛሉ ፤ ነገ በተሻለ የአዕምሮ መነሳሳት ጨዋታውን ለማድረግ ዝግጁ ነን።”

ከነገው ጨዋታ ምን ይጠብቃሉ…?

“ፋሲል ከነማ ጠንካራ ተጋጣሚ እንደሚሆን እንጠብቃለን። ፋሲል ከነማ ጠንካራ ስብስብ ያለው ጥሩ እግርኳስ የሚጫወት ቡድን ነው። በመሆኑም ጠንካራ ፉክክር እንደሚጠብቀን እናምናለን ፤ ለዚህም አዕምሯችንን ዝግጁ ማድረግ ይገባናል።”

ዘግይተው ባህር ዳር ስለመግባቸው…?

“ከእኛ ውጤት ይፈልጋሉ። ግን የሚጠብቁትን ያህል እየሰሩ አይደለም። በረራም ከዛሬ በፊት ማግኘት አልቻልንም። ለዚህም ነው የዘገየነው።”