ባህር ዳር ከተማ አሠልጣኙን ይፋ አደረገ

ከትናንት በስትያ ሶከር ኢትዮጵያ የጣና ሞገዶቹ አሠልጣኝ ለመሆን ከጫፍ ደርሰዋል ያለቻቸው አሠልጣኝ ደግአረገ ይግዛው በይፋ ቡድኑን ተረክበዋል።

ኢንስትራክተር አብርሃም መብራቱ የፊፋ የቴክኒክ ኤክስፐርት ሆነው መመረጣቸውን ተከትሎ አሠልጣኙ ቀሪ የአንድ ዓመት ውል ቢኖራቸውም ከቡድኑ ጋር እንደማይቀጥሉ መገለፁ ይታወቃል። በእርሳቸው ምትክ ክለቡ ሦስት አሠልጣኞችን እያጤነ እንደነበረ እና አሠልጣኝ ደግአረገ ይግዛውን ለመሾም ከጫፍ እንደደረሱ ከትናንት በስትያ ዘገባ ማቅረባችንም ይታወቃል። አሁን ክለቡም አሠልጣኙን መሾሙን በይፋ አስታውቋል።

የቀድሞ የአውሥኮድ እና ኢኮሥኮ አሠልጣኝ ደግአረገ 2012 እና 2013 የውድድር ዓመትን በወልቂጤ ከተማ ያሳለፉ ሲሆን ዓምና ደግሞ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የአሠልጣኝነት ህይወታቸውን መቀጠላቸው አይዘነጋም። አሁን ደግሞ በሊጉ ዳግም ለማሰልጠን የሦስት ዓመት ውል ፈርመው የትውልድ ከተማቸውን ክለብ ተቀላቅለዋል።