የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር 3ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በሀያት ሪጀንሲ ሆቴል ሲካሄድ የተነሱ ሀሳቦች…

👉 “የቫርን ጉዳይ ለጊዜው አቁመነዋል..

👉 “በዳኞች በኩል አንዳንድ ስህተቶች በፍፁም ሆን ተብሎ የተፈፀሙ በሚመስል መልኩ የሚፈፀሙ ናቸው…


👉 “የዚህ ዓመት ውድድር መዝጊያችን አዲስ አበባ ነው የሚሆናው…

የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ዮሐንስ ጥላሁን በክብር እንግድነት በታደሙበት በዚህ መድረክ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር የቦርድ ሰብሳቢ መቶ አለቃ ፍቃደ ማሞ በ2015 ሊሰሩ ስለታሰቡ ጉዳኞች ዙርያ ተከታዮዩን ማብራሪያ ለጉባየተኛው ሰጥተዋል።

“ኤጀንቶች(ደላሎች) ትኩረታቸው የሀገራችን ተጫዋቾች ላይ አድርገዋል። አበቡበከር ናስር የዚህ ውጤት መሆኑን እና በቀጣይም በርከት ያሉ ተጫዋቾች ይህን እድል ያገኛሉ። አባላቶች ባነሳችሁት ሀሳብ መሠረት አክሲዮን ማህበሩ በንብረት እረገድ ሀሳቴ እያፈራ መጥቷል የራሱ ንብረቶችን እያገኘ ነው። በ2014 የውድድር ዘመን በአነስተኛ እና በከፍተኛ ሁኔታ ችግሮች አጋጥመውት አልፈዋል። ከእዚህም መካከል በዳኝነት በኩል የሚፈጠሩ ስህተቶች ቅፅበታዊ እና ከዳኛው ችሎታ ጋር የሚገናኝ በመሆኑ በቅን ልቦና የተፈፀሙ ስህተቶች ይሆናሉ ብለን እናምናለን። አንዳንድ ስህተቶች በፍፁም ሆን ተብሎ የተፈፀሙ በሚመስል መልኩ የሚፈፀሙ ናቸው። እነዚህ ነገሮች እንዳይደገሙ ዘንድሮ ከኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ጋር በትኩረት የመንነጋገርባቸው አንዱ ጉዳያችን ነው። ሌላው የገጠመን ፈተና የውድድሩን አሸናፊ አንገት ለአንገት የተናነቁበት እና ወራጆቹም እስከ መጨረሻው ድረስ ያልታወቁበት የውድድር ዘመን ነበር። የመጨረሻ ሳምንት ጨዋታዎችን በተለያዩ ሜዳዎች በእኩል ሰዓት እንዲካሄዱ ተደርጓል። ያም ቢሆን አንዱ ለቆብኛል፣ ተንኮል ተሰርቶብኛል እና ያለ አግባብ ድርጊት ተፈፅሞብኛል የሚል ክስ ቀርቦልናል። ያደረግነው የጨዋታው ኮሚሽነር እና ዳኞች ጠርተን አነጋግረናል። በቀረበው ክስ መሠረት ተፈፀመ የተባለውን ነገር የሚያሳይ ማስረጃ ባናገኝም ለወደፊቱ እንዲህ ያሉ ነገሮች ሲያጋጥሙን በውድድር ደንባችን ይህንን መቆጣጠር የሚያስችል አዲስ ደንብ ተዘጋጅቷል ተወያይተንበት የሚፀድቅ ይሆናል። የሊጉ አክሲዮን ራሳችንን ከሱፐር ስፖርት ጋር ሰፊ ገምግመናል በግምገማችን ከኮቪድ በኋላ ተመልካች ወደ ሜዳ እንዲገቡ ቢፈቅድም ውድድሮቹ የሚካካሄዱበት መንገድ በሜዳ እና ከሜዳ ውጭ በሚለው ከማድረግ ይልቅ በተመረጡ አምስት ከተሞች ማድረጉን መልካም መሆኑን ተስማምተናል። በዚህም መሠረት ዘንድሮ በአምስት በተመረጡ ከተሞች ውድድሮቻችንን እናካሂዳለን።

እንዲሁም በቀጥታ የቴሌቭዠዥን ስርጭቱ ወቅት የሚታየው ሎጎ (አንድ ሰው ኳስ ሲመታ የሚያሳየው) እና የመግቢያ ሙዚቃው እንዲቀየር ሰፊ ክርክር እና ውይይት በማድረግ እንዲቀየር አድርገናል። ከዚህ በተጨማሪ ልዩ ልዩ ስልጠናዎችን ለአሰልጣኞች፣ ለዳኞች፣ ሚዲያ አካላት እና ለክለብ አመራሮች ሰጥተናል። በዚህም ከአንድ ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ አውጥተናል። ሆኖም ግን በክለብ አመራሮች ስልጠና የሚላኩ ሰዎች ከሌላ የስራ ዘርፍ የሚመጡ መሆናቸው ለስልጠናው የማይመጥኑ በመሆናቸው በቀጣይ ትክክለኛ ተወካይ የማይመጣ ከሆነ አንቀበልም። የዘንድሮ ውድድር በባህር ዳር፣ ድሬዳዋ ፣ አዳማ እና በመጨረሻም አዲስ አበባ እናደርጋለን። ሀዋሳን አመቱን ሙሉ ሜዳውን እንዲያስተካክሉ በተደጋጋሚ ገልፀናል። ኮሚቴም ሄዶ ተነጋግሯል። እነርሱም ሜዳውን እንደሚያስተካክሉ ነግረውናል ከተሰራ እና ካለቀ ሀዋሳ ልንሄድ እንችላልን። ሆኖም ግን የዚህ ዓመት ውድድር መዝጊያችን አዲስ አበባ ነው የሚሆናው። ከዚህ ቀደም አንድ ሜዳን ለመምረጥ መመዘኛችን ሆቴል ፣ ጥሩ መጫወቻ ሜዳ እና ፀጥታ ነበር። አሁን ግን ተመልካች አግባቡ መገኘት ስለሚገባ አንዱ መለኪያ የተመልካች ብዛት ሆኗል። ስለዚህ ውድድሩ የሚካሄድባቸው ከተሞች ተመልካች ወደ ስታዲየም እንዲመጣ ከፍተኛ ቅስቀሳ ማድረግ ያስፈልጋል። ውድድሩ እየተካሄደ ተመልካች የሌለው ከሆነ ውድድሩን አቋርጠን ተመልካች ወደሚገኝበት ከተሞች የምንሄድ መሆኑን አስረግጠን እንናገራለን።

በ2015 ለመስራት ካሰብናቸው ውሰጥ 160 ጨዋታዎችን በቀጥታ ለመስተላለፍ ነው። ሆኖም ብዙ ክርክር አስነስቷል። በቀጣይ ብዙ ውይይት የሚያስፈልገው በመሆኑ ከውድድሩ ጅማሮ አስቀድሞ የቀጥታ ስርጭት ሽፋን የሚያገኙ የጨዋታ ብዛቶችን የምናቀው ይሆናል። ሌላው ገቢ ለማግኘት በስታዲየሞቹ ማስታወቂያ ለመስራት ዲጅታል የማስታወቂያ ሰሌዳ ወደ ሀገራችን ለማምጣት ጥረት እየተደረገ ነው። ይሄም ይሳካል ብለን እናምናለን። ተጨማሪ ገቢም ያስገባልናል። የቪዲዮ ምስልን(ቫርን) በዚህ ዓመት ለማድረግ ጨረታ አውጥተን ነበር። ሁለት ድርጅቶችም ተወዳድረው ነበር። ሆኖም ግን ከወጪ አንፃር እንዲሁም ካገኘነው ምክረ ሀሳብ በመነሳት ጫናው ከባድ በመሆኑ በዚህ ዓመት የቫርን ጉዳይ ለጊዜው አቁመነዋል።”