በወንድማገኝ ኃይሉ እና በሀዋሳ ከተማ መካከል ያለመግባባት ተፈጥሯል

ያለፉትን ሁለት ዓመታት በሊጉ ጎልቶ የወጣው ወንድማገኝ ኃይሉ ከአሳዳጊ ክለቡ ጋር ውዝግብ ውስጥ ገብቷል።

ሀዋሳ ከተማን ከታችኛው ቡድን በማደግ ለተከታታይ ሁለት የውድድር ዘመናት ያገለገለው ወጣቱ አማካይ ከሀዋሳ ከተማ ጋር ያለው የውል ጊዜ ዕክል ገጥሞታል። የውዝግቡ መነሻ ሀዋሳ ከተማ ከ2013 እስከ 2016 ጥቅምት 30 ቀን ድረስ ለሦስት ዓመት የሚያቆየው የውል ስምምነት እንዳለው በመግለፅ የክርክር መነሻቸውን ሲያቀርቡ በአንፃሩ ተጫዋች ወንድማገኝ በበኩሉ ‘የውል ዘመኔ የሚጠናቀቀው በ2015 ጥቅምት 30 ነው’ በማለት የሰነድ ማስረጃ በመያዝ የእግርኳሱ የበላይ አካል ወደ ሆነው ፌዴሬሽን ቀርበዋል። ፌዴሬሽኑ በቅርቡ በሁለቱ አካላት መካከል ለተፈጠረው ውዝግብ የመጨረሻ ዕልባት እንደሚሰጥ ይጠበቃል።

በኢትዮጵያ እግርኳስ ውስጥ በአጭር ጊዜ ከወጣት ቡድን በማደግ በፕሪምየር ሊጉ ማንፀባረቅ ከቻሉ ተጫዋቾች መካከል አንዱ የሆነው ወጣቱ የአማካይ ስፍራ ተጫዋች ወንድማገኝ የሀዋሳን ከ17 እና ከ20 ዓመት በታች ቡድን ካገለገለ በኋላ በ2013 የዋናውን ቡድን በመቀላቀል በቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ላይ ጎልቶ መውጣት ችሏል፡፡