ሀዲያ ሆሳዕና ምክትል አሠልጣኝ ሾሟል

ከዚህ ቀደም ሁለት ጊዜ ክለቡን በዋና አሠልጣኝነት የመሩት አሠልጣኝ ግርማ ታደሰ በምክትል አሠልጣኝነት ሚና ዳግም ክለቡን መቀላቀላቸው ታውቋል።

በይፋ ከአሠልጣኝ ሙሉጌታ ምህረት ጋር የመለያየቱ ነገር በግልፅ ያልታወቀው ሀዲያ ሆሳዕና በምክትል አሠልጣኙ ያሬድ ገመቹ የረዳት ጊዜያዊ አሠልጣኝነት ሚና እየተመራ የዘንድሮውን የውድድር ዓመት መጀመሩ ይታወቃል። ክለቡ ከዋና አሠልጣኝነት ጋር በተያያዘ እስካሁን ምንም ጉዳይ ባያወጣም አዲስ ምክትል አሠልጣኝ ማግኘቱ ግን ተረጋግጧል።

ሁለተኛ ምክትል አሠልጣኝ የሆኑት ግርማ ታደሠ ናቸው። 2007 እና 2011 ላይ ክለቡን ከከፍተኛ ሊግ ወደ ፕሪምየር ሊግ ያሳደጉት አሠልጣኙ 2012 ላይ በውጤት ማጣት ምክንያት ከክለቡ ጋር ተለያይተው እንደነበር አይዘነጋም። የቀድሞ የደቡብ ፖሊስ፣ ስልጤ ወራቤ እና ሀምበሪቾ ዱራሜ አሠልጣኝ ከትናንት በስትያ ወደ ባህር ዳር ተጉዘው ስብስቡን ቢቀላቀሉም ህጋዊ ወረቀቶች ግን አሁን ረፋድ ላይ መገባደዳቸው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።