ከፍተኛ ሊግ | ጅማ አባቡና አዲስ አሰልጣኝ ሾሟል

2009 ላይ ወደ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አድጎ ወዲያው የወረደው ጅማ አባቡና አዲስ አሠልጣኝ አግኝቷል።

በቴዎድሮስ ታደሠ

ጅማ አባቡና 2009 ላይ ወደ ፕሪምየር ሊጉ አድጎ በዓመቱ ወደመጣበት ሊግ ከወረደ በኋላ ያለፉትን አምስት ዓመታት በከፍተኛ ሊጉ ተሳትፎን እያደረገ የሚገኝ ሲሆን ዘንድሮ ከሊጉ ቢወርድም የተሳታፊ ክለቦች ቁጥር በመጨመሩ በሊጉ እንደሚቀጥል መረጋገጡ ይታወቃል። ባለፉት ዓመታት በፋይናንስ እና አስተዳደራዊ ችግሮች ውስጥ የከረመው ክለቡም ለ2015 የውድድር ዘመን ከወዲሁ ራሱን ማደራጀት ጀምሮ አዳዲስ ዋና እና ረዳት አሠልጣኞች ቀጥሯል።

በዚህም ከዚህ ቀደም አዳማ ከተማን በረዳት ከዛም በዋና አሠልጣኝነት የመሩት አስቻለው ኃይለሚካኤል የዋና አሰልጣኝነት ኃላፊነት ሲረከቡ ታዳጊና ወጣት ተጫዋቾችን በማብቃት የረዥም ጊዜ ልምድ ያለውን አሰልጣኝ ጋሻው መኮንን እና ያሳለፍነው ዓመት ከበደሌ ከነማ ጋር ጥሩ ጊዜ ያሳለፈውን ወጣቱን አሰልጣኝ ይሳቅ ረጋሳን በምክትል አሰልጣኝነት ሾሟል ።