ወላይታ ድቻ ሥራ አስኪያጅ ሾሟል

ወላይታ ድቻ የቀድሞው ሥራ አስኪያጁን ወደ ኃላፊነት አምጥቷል።

በቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የ2015 የውድድር ዘመን አጀማመራቸው ካላማሩ ክለቦች መካከል አንዱ ወላይታ ድቻ ይጠቀሳል፡፡ ካደረጋቸው ሦስት ጨዋታዎች በሁለት አቻ እና በአንድ ሽንፈት በደረጃ ሰንጠረዡ 15ኛ ላይ ተቀምጦ የሚገኘው ክለቡ የቀድሞው ስራ አስኪያጁን ወደ መንበሩ በድጋሚ መልሷል፡፡

በቅርቡ የክለቡ ሥራ አስኪያጅ የነበሩትን አቶ ወንድሙ ሳሙኤልን ከቦታው ያነሳው በተለያዩ ጊዜያትም ሥራ አስኪያጆችን ሲለዋውጥ የሚታየው ወላይታ ድቻ በሊጉ እያስመዘገበ ካለው ውጤት እንዲሁም ደግሞ በአስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን ለመድፈን በማሰብ በቦታው አዲስ ሹመት አስፈልጎታል። በዚህም ክለቡን ከምሰረታው ጀምሮ እስከ 2012 ድረስ በሥራ አስኪያጅነት እና በቡድን መሪነትም ጭምር ሲመሩ የነበሩትን እና በአሁኑ ሰዓት የፕሪምየር ሊጉ አክሲዮን ማህበር የቦርድ አባል የሆኑትን አቶ አሰፋ ሆሲሶን በቀደመው የሥራ አስኪያጅነት ቦታ መመለሱን ለሶከር ኢትዮጵያ በላከው መረጃ አመላክቷል፡፡