ከፍተኛ ሊግ | ሰበታ ከተማ አዲስ አሰልጣኝ ሾሟል

ከቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ወደ ታችኛው የሊግ ዕርከን የወረደው ሰበታ ከተማ አዲስ አሰልጣኝ ቀጥሯል፡፡

በ2014 ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ተሳትፎን ያደረገው እና በዓመቱ መጨረሻም ከውጤት ማጣት እና ከአስተዳደራዊ ጉዳዮች ጋር እየታገለ በመጨረሻም ወደ ከፍተኛ ሊግ የወረደው ሰበታ ከተማ የዘንድሮውን የከፍተኛ ሊግ ውድድርን ከመጀመሩ አስቀድሞ የአዲስ አሰልጣኝ ቅጥርን ፈፅሟል፡፡ ታዬ ናኒቻም አዲሱ የክለቡ አሰልጣኝ ሆነዋል፡፡

ሰበታ ከተማን ከዚህ ቀደም በቴክኒክ ዳይሬክተርነት እና በሥራ አስኪያጅነት ማገልገል የቻሉት አሰልጣኙ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽን የቴክኒክ ኮሚቴ አባል እንዲሁም ደግሞ አርሲ ነገሌን ከ2012 እስከ 2013 ድረስ በዋና አሰልጣኝነት ያገለገሉ ሲሆን ባሳለፍነው ዓመትም በኢትዮ ኤሌክትሪክ የቴክኒክ ዳይሬክተርነት ቦታ ላይ ከሰሩ በኋላ ወደ ቀድሞው ክለባቸው ሰበታ ከተማ በዋና አሰልጣኝነት በይፋ መሾማቸውን ሶከር ኢትዮጵያ ከክለቡ ያገኘችው መረጃ ያመላክታል፡፡