ከፍተኛ ሊግ | ወልዲያ ከተማ አዲስ አሰልጣኝ ቀጥሯል

በፀጥታ ችግር ምክንያት በተጠናቀቀው ዓመት በከፍተኛ ሊጉ መሳተፍ ያልቻለው ወልዲያ ከተማ በይፋ አዲስ አሰልጣኝ ቀጥሯል፡፡

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የተሳትፎ ታሪክ ካላቸው ቡድኖች መካከል አንዱ የነበረው ወልዲያ ከተማ ወደ ከፍተኛ ሊጉ ከወረደ በኋላ እስከ 2013 የውድድር ዘመን ድረስ በሊጉ ሲሳተፍ ቆይቷል፡፡ በተጠናቀቀው የውድድር ዓመት ግን በአካባቢው በተፈጠረ የፀጥታ ችግር ምክንያት መሳተፍ ሳይችል መቅረቱ ይታወሳል፡፡ ክለቡ በዘንድሮው የ2015 የከፍተኛ ሊግ ውድድር ላይ ተጠናክሮ ለመቅረብ ከቀናት በፊት የአሰልጣኝ ቅጥር ማስታወቂያን ማውጣቱ የሚታወስ ሲሆን ይህን መሠረት በማድረግም ካሊድ መሐመድን ዋና አሰልጣኝ በማድረግ ቀጥሯል፡፡

ኢትዮጵያ ቡና በረዳት እና ጊዜያዊ አሰልጣኝ በመሆን ማሰልጠን ከጀመረ በኋላ በዳሽን ቢራ በፕሪምየር ሊግ ደረጃ በኢትዮጵያ መድን ፣ ቡታጅራ ከተማ እና ሀላባ ከተማ ደግሞ በከፍተኛ ሊጉ አሰልጣኝ በመሆን የሰራው አሰልጣኙ ቀጣዩ የወልዲያ አዲሱ አሰልጣኝ በመሆን በይፋ ተቀጥሯል፡፡