ኢትዮ ኤሌክትሪክ በአሰልጣኞቹ ላይ ውሳኔ አሳልፏል

ዋና አሰልጣኙን እና የግብ ጠባቂዎች አሰልጣኙን ወደ መዲናዋ የጠራው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ውሳኔ አስተላልፏል።

በትናትናው ዘገባችን ኢትዮ ኤሌክትሪክ የቡድኑን ዋና አሰልጣኝ ክፍሌ ቦልተናን እና የግብ ጠባቂዎች አሰልጣኝ መሐመድን በስልክ ጥሪ ሪፖርት እንዲያደርጉ ወደ አዲስ አበባ እንደጠራቸው እና አሠልጣኞቹ ዛሬ ሪፖርት እንደሚያቀርቡ ገልፀን ነበር። ዛሬ ሪፖርቱን ለማዳመጥ ስብሰባ የተቀመጠው የክለቡ ስራ አመራር ቦርድ ውሳኔ ማሳለፉን ሶከር ኢትዮጵያ አውቃለች።

በዚህም መሠረት አሰልጣኝ ክፍሌ ቦልተና ክለቡ ካለበት ደረጃ እንዲሻሻል ከክለቡ አመራሮች ጋር ውይይት አድርገው ወደ ድሬዳዋ እንዲመለሱ የተደረገ ሲሆን የግብ ጠባቂዎች አሰልጣኝ መሐመድን ግን ወደ ተስፋ ቡድን ወርደው እንዲሰሩ ውሳኔ ተላልፏል።