የአሰልጣኞች አስተያየት | ሲዳማ ቡና 2-4 ፋሲል ከነማ

👉”ተጫዋቾቻንን በጣም ጥሩ ነበሩ ፤ ማሸነፍ አይበዛባቸውም” ኃይሉ ነጋሽ

👉”ጨዋታው ከጅምሩ በዚህ መልክ ያቀድነው አይደለም” ሥዩም ከበደ

አሰልጣኝ ኃይሉ ነጋሽ – ፋሲል ከነማ

ስለ ጨዋታው…

ዛሬ በጠበቅነው መልኩ ነው የሄደው ፣ የበቀደሙ አሸናፊነታችን ከጭንቀት ስላወጣን በነፃነት ነው ዛሬ ተጫዋቾቻችን የተጫወቱት። ተጫዋቾቻንን በጣም ጥሩ ነበሩ ፤ ማሸነፍ አይበዛባቸውም፡፡

ስለ ሱራፌል ዳኛቸው መመለስ

ጨዋታው የሚታይ ነው፡፡ ባለፈውም ተቀይሮ ገብቶ ጥሩ ነገር ነው ለክለቡ ያደረገው ፣ ዛሬም እስከነበረበት ሰዓት የእርሱ እያንዳንዱ ኳሶች በጣም ለእኛ አስፈላጊዎች ነበሩ፡፡ ስለዚህ ጥሩ ነበር እንቅስቃሴው፡፡

በሚፈለገው ደረጃ ቡድኑን ሰለ ማግኘታቸው

ገና ነው ፤ ማለት ሁሉም ነገር የሚስተካከለው በአሸናፊነት ነው፡፡ ፋሲል ሁሌም አሸናፊ ነውና አንዳንዴ ስትሸነፍ ተጫዋቾች ያንን ነገር ያጡብሀል። ከእዛ አኳያ ነው አጥተን የነበረው ፤ አሁን በአሸናፊነት ብዙ ነገሮችን እያስተካከልክ ትሄዳለህና ተጫዋቾቻችን ያለውን ጥረታቸውን አድርገዋል። ድሉም ይገባቸዋል ማለት እፈልጋለሁ፡፡

አሰልጣኝ ሥዩም ከበደ – ሲዳማ ቡና

ስለ ጨዋታው…

ጨዋታው ከጅምሩ በዚህ መልክ ያቀድነው አይደለም። ይሄንን ጨዋታ የበለጠ ካለፈው ከመቻል ውጤት መነሳሳት ጀምሮ ሳምንቱን ያሳለፍነው ጥሩ ነበር። ዛሬም ውጤት ይዘን እንወጣለን የሚል እጅግ ተስፋ ሰንቀን ነው የገባነው ፤ ግን ከተጀመረ 5 ደቂቃ ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የተገኘው የፍጹም ቅጣት ምት ብዙዎቻችንን ረብሾናል። የፋሲልን ተጫዋቾችም የበለጠ ማነሳሳት ችሏል። የእኛም አልፎ አልፎ ያልተቀናጁ ነገሮች ይታዩ ነበር። በዛ መካከል ደግሞ እንደዚሁ አጠር ባለ ሰዓት አሁንም የተከላካይ የመግባባት ስህተት ሁለተኛ ጎል ሲቆጠር ብዙ ነገሮችን አበላሽቷል። በአጠቃላይ የነበረው የመጀመሪያ አጋማሽ ልክ አልነበረም። ዕረፍት ላይ የተነጋገርነው ሦስት ነገሮችን ነው ፤ ከቻልን በኳስ የማይቻል ነገር የለምና ማሸነፍ ይቻላል፣ ካልሆነ ነጥብ መጋራት አለብን ፣ ካልሆነ የጎሉ ልዩነት መጥበብ አለበት የሚል ነበር። ገና ብዙ ውድድሮች ብዙ ተፎካካሪነት ስላለን ከዛ አኳያ ተጫዋቾቹ እንዲረጋጉ በደንብ የሚቻለውን ማድረግ እንደምንችል ተነጋግረን ገብተናል። ቢያንስ ሁለተኛው አጋማሽ ይሻላል። ዞሮ ዞሮ ግን ለቀጣይ ውድድሮች ደግሞ የሚታረሙ እና የሚስተካከሉ ነገሮች ሁሉ በእያንዳንዱ ጨዋታ ላይ ስላሉ እነዛን እያስተካከልን ለቀጣይ ብዙ ነገሮችን ሠርተን ተደራጅተን የተሻለ ቡድን ሆነን እንቀርባለን ብዬ አስባለሁ።

እንደ ቡድንም ሆነ በተናጥል በተጫዋቾች ላይ ስለሚታየው የወጥነት ችግር…

እሱ ነው ችግሩ! ሁሌ ጨዋታ ስታስኬድ  ሁሌ የምላቸው ነው የመጀመሪያ 15 ደቂቃ እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው። ያንን ተቆጣጥረህ ከቻልክ ተጋጣሚህን በጎል መብለጥ ካልሆነ ወደ ጨዋታው ስሜት ውስጥ ለመግባት ጥረት ማድረግ ይሄ ሲሆን አንዳንድ ጊዜ ደግሞ በችሎታቸው የላቁ ተጫዋቾች ያስፈልጋሉ። የሚሳሳቱ ልጆች አሉ። ይሄ በሂደት ነው የምታርመው። ስለዚህ የእኛ መቻል ላይ የነበረንን የተሰቀለውን ስሜታችንን  አሁንም ማስቀጠል ሲገባን እንደገና ላይ እና ታች መሆኑ ይሄ ደግሞ የበለጠ በጥሞና ልንሠራ የሚገባን ነውና እነዚህን ሁሉ እናስተካክላለን ብዬ አስባለሁ።