ከፍተኛ ሊግ | ንብ ቡድኑን በማጠናከር ዝግጅቱን አጠናቋል

ንብ በሚል የቀድሞው አንጋፋ ስያሜው በከፍተኛ ሊጉ ላይ የሚካፈለው ክለብ በተለያዩ አዳዲስ ተጫዋቾች ራሱን በማጠናከር ዝግጅቱን አገባዷል፡፡

ዘለግ ካለ ዓመታት በኋላ የመከላከያ ቢ ቡድን ወደ ከፍተኛ ሊጉ ማደጉን ተከትሎ በተመሳሳይ ስያሜ አንድ ቡድን መቀጠል አይችልም በሚለው መመሪያ መሰረት አየር ኃይል በቀድሞው መጠሪያ ስያሜው ንብ በሊጉ እንደሚካፈል ይታወቃል። ክለቡ አሰልጣኝ ደምሰው በፍቃዱን በዋና አሰልጣኝነት ከወር በፊት የቀጠረ ሲሆን ለውድድር በቢሾፍቱ ከተማ ዝግጅቱን ቀጥሏል፡፡ 

ፍሬው ብርሀንን በረዳት አሰልጣኝነት ደጉ ደሳለኝን በግብ ጠባቂ አሰልጣኝነት የሾመ ሲሆን ስምንት የወታደር ተጫዋቾችን የስብስቡ አካል ካደረገ በኋላ ወደ 18 የሚጠገቡ ተጨማሪ አዳዲስ ተጫዋቾችን ደግሞ ከተለያዩ ክለቦች በይፋ በማስፈረም ዝግጅቱን አጠናክሮ ቀጥሏል፡፡

ዋኬኒ አዱኛ ግብ ጠባቂ ከአዲስ አበባ ከተማ ፣ የቀድሞው የድሬዳዋ ከተማ እና ስልጤ ወራቤ አማካይ ረመዳን ናስር ፣ የቀድሞው የወላይታ ድቻ እና ጅማ አባጅፋር አማካይ አማኑኤል ተሾመ ፣ በሀዋሳ ከተማ ወጣት ቡድን ውስጥ በተከላካይ ስፍራ ላይ ያገለገለው ወጣቱ ዳግም ወንድሙ ፣ በሀምበሪቾ ዱራሜ እና አምና በሀላባ ያሳለፈው አማካዩ ንስሐ ታፈሰ ፣ በአዲስ አበባ ከተማ አምና ያሳለፉት ግብ ጠባቂው ኮክ ኩዌት እና ተከላካዩ ቧይ ጆን እንዲሁም ከመከላከያ የተገኘው ኪም ላም ከንግድ ባንክ ወጣት ቡድን ናትናኤል ሰለሞን ፣ የቀድሞው የጅማ አባ ቡና ተጫዋች ፉአድ ተማምን ጨምሮ አሸናፊ ጉታ ፣ አያልቅበት ነጋዎ ፣ ፉዓድ ሙዘሚል ፣ ኪያር መሀመድ ፣ ኩራባቸው ቢዘልቅ ፣ አዲስ ፍሰሀ ፣ ለምለም ግርማ እና ከፍያለው ካስትሮ የክለቡ አዳዲስ ፈራሚዎች ናቸው፡፡