\”በወረቀት ላይ የጊኒ ተጫዋቾች የሚጫወቱበትን ሀገር አይተህ ልዩነት ሊኖር ይችላል ብለህ ታስባለህ ፤ ዋናው ግን ሜዳ ላይ ያለው ብቃት ነው\” ዑመድ ኡኩሪ

በኦማን ሊግ በጥሩ ወቅታዊ ብቃት ላይ የሚገኘው ዑመድ ኡኩሪ ከነገው ጨዋታ በፊት ተከታዩን አስተያየት ሰጥቶናል።

ከረጅም ጊዜ በኋላ ወደ ብሔራዊ ቡድን ስለመመለሱ…

ልክ ነው! ከረጅም ጊዜ በኋላ ነው በብሔራዊ ቡድን ድጋሜ ጥሪ የተደረገልኝ። እንደማንኛውም ሰው ጥሪ ሲደረግልኝ በጣም ደስ ብሎኛል። መጥቼ ደግሞ ዛሬ ነው ከቡድኑ ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ ልምምድ የሰራሁት። ያለውም መንፈስ በጣም ደስ የሚል ነው።

\"\"

ስለመጀመሪያው ልምምድ…

ደስ የሚል ስሜት ነው ያለው። እንዳያችሁት ደስ የሚል ልምምድ ነው የሰራነው። በቡድኑ ውስጥም ደስ የሚል ስሜት ነው ያለው።

ስለጊኒው ጨዋታ…

የጊኒው ጨዋታ በጣም ተጠባቂ ነው። ምድቡን በአንደኝነት እየመራን ነው። በሁለቱ የጊኒ ጨዋታ ደግሞ ጥሩ ነገር አድርገን የበለጠ ምድቡን ለመምራት ዝግጁ ነን ብዬ አስባለው።

ስለተጋጣሚያቸው ጊኒ ተጫዋቾች ደረጃ…

በወረቀት ላይ የጊኒ ተጫዋቾች የሚጫወቱበትን ሀገር አይተህ ልዩነት ሊኖር ይችላል ብለህ ታስባለህ ፤ ዋናው ግን ሜዳ ላይ ያለው ብቃት ነው። በውጪ ሀገር የሚጫወቱ በርካታ ተጫዋቾች እነሱ ቢኖራቸውም ሜዳ ላይ በተደራጀ ሁኔታ የምታደርገው ነገር ነው ውጤት ሊያመጣልህ የሚችለው።



እንደቡድንም ሆነ በግል ከጊኒው ጨዋታ ስለሚጠበቅ ነገር…

እኔ በማንኛውም ሰዓት ዝግጁ ነኝ ፤ በማንኛውም ሰዓት ጥሩ ነገር ለመስራት ዝግጁ ነኝ። በግልም ሆነ ከቡድን አጋሮቼ ጋር ጥሩ ነገር ለመስራት ከፈጣሪ ጋር እናስባለን። ወደብሔራዊ ቡድን ጥሪ ሲደረግልኝ ከእኔ ምን እንደሚጠበቅ ይታወቃል። ለዚህም በሥነ-ልቦናም ሆነ በአካል ዝግጁ ነኝ።

ከመጫወቻ ሜዳ ጋር ተያይዞ…

እኛ ሀገር የመጫወቻ ሜዳ ብዛት ነው ያለው እንጂ ጥራት የለም ፤ አሁን እዚህ (ሞሮኮ) እንዳየነው አይደለም። ሜዳዎች መሰራት ያለባቸው በዚህ ደረጃ ነው ብዬ አስባለው። የፊፋ እና ካፍን መስፈርት በሚያሟላ ሁኔታ ማለት ነው። ለዚህም ነው ብሔራዊ ቡድናችን በሜዳው መጫወት ያልቻለው።

\"\"