ኢትዮ ኤሌክትሪክ በዝውውሩ በንቃት መሳተፉን ቀጥሏል

በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ ተጠናክሮ ለመገኘት ከሰሞኑ ዝውውሮችን እየፈፀመ የሚገኘው ኤሌክትሪክ ሦስት አዳዲስ ተጫዋቾች በማስፈረም የአዳዲሶችን ቁጥር አስራ ሦስት አድርሷል።

በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ ላይ ጠንካራ ከሆኑ ጥቂት ክለቦች መካከል አንዱ የሆነው የአሰልጣኝ መሠረት ማኔው ክለብ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሦስት አዳዲስ ተጫዋቾችን በዛሬው ዕለት በማስፈረም የአዳዲስ ፈራሚያቸውን ቁጥር አስራ ሦስት አድርሰዋል።

ክለቡን የተቀላቀለችው አጥቂዋ ፀጋነሽ ወራና ነች። በአርባምንጭ ከተማ የእግር ኳስ ህይወቷን ከጀመረች በኋላ በመቀጠል በድሬዳዋ ከተማ እንዲሁም ያለፈትን ሁለት ዓመታት በንግድ ባንክ ካሳለፈች በኋላ ቀጣይ መዳረሻዋ ኤሌክትሪክ ሆኗል።

ሌላኛዋ ፈራሚ የመስመር አጥቂዋ የምስራች ላቀው ናት። ከአርባምንጭ መነሻዋን ካደረገች በኋላ በመቻል ፣ አዳማ እንዲሁም ለተከታታይ ሦስት ዓመታት ከንግድ ባንክ ጋር ማሳለፏ ይተወሳል።

የክለቡ አስራ ሦስተኛ ፈራሚ የሆነችው አብነት ለገሠ በአዲስ አበባ ከተማ የተጠናቀቀውን ዓመት በድሬዳዋ ከተማ ተጫውታ ቆይታ ቀጣዩ ክለቧ ኢትዮ ኤሌክትሪክ መሆኑ ተረጋግጧል።