የቀድሞ የወልቂጤ ከተማ ተጫዋች ቅጣቱን ጨርሶ አዲስ ክለብ ተቀላቅሏል

ለአጭር ጊዜም ቢሆን ወልቂጤ ከተማን ያገለገለው የግብ ዘብ በፊፋ የተጣለበትን ቅጣት አገባዶ ወደ እግርኳስ ተመልሷል።

የ2014 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ከመጀመሩ በፊት ወልቂጤ ከተማን የተቀላቀለው አይቮሪያዊው የግብ ዘብ ሲልቫይን ግቦሆ በሊጉ 8 ጨዋታዎችን (699 ደቂቃዎችን)ከተጫወተ በኋላ በወቅቱ እንደተገለፀው ኖቬምበር ላይ በዓለም ዋንጫ ማጣርያ አይቮሪኮስት ከጋቦን ጋር ስትጫወት በእጣ የዶፒንግ ምርመራ እንዲሰራለት ወጥቶበት የሽንት ናሙና ሰጥቶ በናሙናው ውስጥም ትራይሜታዚዲን የሚባልና ከ2014 ጀምሮ አትሌቶች እንዳይጠቀሙት በዋዳ የታገደ ንጥረ ነገር ተገኝቶበት በፊፋ እግድ ተጥሎበት አንደነበረ አይዘነጋም። ተጫዋቹ ያለፉትን 18 ወራት ከእግርኳስ ከራቀ በኋላም በዚህ ሳምንት ቅጣቱን ጨርሶ አዲስ ክለብ ማግኘቱ ታውቋል።

ከሀገሩ ጋር 2015 ላይ የአፍሪካ ዋንጫን ያነሳው ግቦሆ በአይቮሪኮስ ሊግ ኧ ሎናሲ ለሚሳተፈው የዋና ከተማው ክለብ ስታድ ደ አቢጃን የአንድ ዓመት ውል በመፈረም ወደ እግርኳስ ዳግም ተመልሷል።