የመቻል የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓል የማጠቃለያ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል

👉 “መቻል የስታዲየም እንዲኖረው እንሰራለን” የክለቡ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ሰይፉ ጌታሁን

በተለያዩ ክንዋኔዎች 80ኛ ዓመት ክብረ በዓላቸውን በደማቅ ሁኔታ ያከበሩት መቻሎች በዝግጅቱ ዙርያ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በመቻል ስፖርት ክለብ ፅህፈት ቤት በተዘጋጀው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የክለቡ የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ሰይፉ ጌታሁን እና የክለቡ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ኮ/ል ደረጄ መንግስቱ ሲገኙ ጥሪ የተደረገላቸው የሚዲያ አካላት በቦታው ተገኝተው ነበር።

የመግቢያ ንግግር ያደረጉት የክለቡ የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ሰይፉ በንግግራቸው “ የዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫ ለመጥራት የተገደድነው በሰማንያ ዓመት ክብረ በዓል ወቅት ከፍተኛ አጋርነት ላሳዩት ለተለያዩ ተቋማት እና የሚዲየ አካላት ምስጋና ለማቅረብ እንደሆነ ተናግረው። ይህ አዲሱ ቦርድ ከመጣ በኋላ ለሰማነኛ ዓመት ክብረ በዓል አከባበር እንሰራቸዋለን ያልነውን ስራዎች ዘጠና ዘጠኝ በመቶ አሳክተናል” ካሉ በኋላ በዋናነት ከ30 ሺህ ህዝብ በላይ የተሳተፈበት ሩጫን፣ ታላላቅ የእግርኳስ ሰዎችን እንደ ናኒ ካኑ በመጋበዝ ክለቡንም ሆነ ሀገርን ማስተዋወቅ የተሻለበት ስራ፣ ከፍተኛ አመራሮች እና ባላሀብት የተገኙበት የዕራት ግብዣ ፕሮግራም ላይ ከአምስት መቶ ሚሊየን ብር በላይ በካሽ ቃል የተገባውን ጨምሮ ወደ አንድ ቢልየን ብር የተገኘበት ዝግጅት ዋነኛ ሰኬት እንደሆነ ገልፀዋል። በቀጣይ የተለያዩ የስፖርት መሰረተ ልማት፣ የሜዳ ስራዎችን እንደሚጀምሩ ገልፀዋል። በአጠቃላይ ዝግጅቱ ባመረ ሁኔታ መጠናቀቁን አንስተው በቀጣይ የመቻልን ዝናና ክብር ለመመለስ የተለያዩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አውስተው በተለይ 30ሺህ ህዝብ የተሳተፈበት የሩጫ ውድድር በየዓመቱ “የመቻል ሩጫ” ተብሎ እንደሚካሄድ ተናግተዋል።


በማስከተል የተናገሩት የክለቡ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ኮ/ል ደረጄ በተመሳሳይ የክለቡን ሰማንያ ዓመት ክብረ በዓል አስመልክቶ ለማከናወን ያሰቧቸውን ዕቅዶች ከግብ ማደረሳቸው ተናግረው ለዚህም መሳካት የክለቡ የቦርድ አመራሮች፣ በክለቡ ስርር የሚገኙ ባለሙያዎች፣ የከተማው አስተዳደር፣ የፀጥታ ክፍሉ እና የሚዲያው ድጋፍ በመሆኑ ከፍተኛ ምስጋና አቅርበዋል። የሰማነኛ በዓሉ ብዙ ትምህርት ያገኘንበት እንደ ሆነ ተናግረው በቀጣይ ለምንሰራቸው ስራዎች የሚዲያው ድጋፍ በጣም አስፈላጊ መሆኑን አንስተው። ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

በቦታው በነበሩ የሚዲያ አካላት ጥያቄዎችን ያነሱ ሲሆን በዋናነት ትኩረት የሚሰበው ጥያቄ ሰማንያ ዓመት ያስቆጠረው መቻል እስከ ዛሬ የስታዲየም አለመገንባቱ ከምን አኳያ እንደሆነ ለተነሳው ጥያቄ የክለቡ ቦርድ ሰብሳቢ ሲመልሱ

“ኢትዮጵያ ውስጥ እግርኳስ የሚወደደውን ያህል በመሰረተ ልማት በስታዲየም ግንባታ በኩል ምንም እንዳልተሰራ ገልፀው። እንደ መቻል ያለ ሰማንያ ዓመት ያስቆጠረ ክለብ ስታዲየም አለመገንባቱ የተነሳው ጥያቄ ትክክል መሆኑን እና ይህ እንዳይሆን የተለያዩ መሰናክሎች በየ ዘመናቱ እንደነበረ አውስተው። ይህ ቦርድ ከመጣ ስምንት ወር ሆኖቷል ከዚህ በኋላ ትልቁ ስራ የሚሆነው የራሱ መለማመጃ ሜዳ፣ የራሱ ስፖርት አካዳሚ እንዲሁም የራሱ የስታዲየም እንዲኖረው ማድረግ ነው። ይህን ወደ ተግባር ለመቀየር ጠንክረው እንደሚሰሩ አንስተዋል። አክለውም ይህ በሀገራችን በቂ የስታዲየም አለመኖር አጠቃላይ የሀገሪቷም ችግር ነው። እኔ በግሌ ብጠይቀኝ የኢትዮጵያ መንግስትን በፊፋ እና በካፍ ሊሸልም ይገባል ባይ ነኝ ምክንያቱም ገንዘብ በጅቶ የስፖርት እንቅስቃሴ እንዲኖር አድርጓል። በሙሉ የክልል ክለቦች በመንግስት በጀቶች እንጂ ክለቦች በራሳቸው የገቢ ምንጭ፣ የስፖርት ንግድ ሲስተም ፈጥረው የሚንቀሳቀሱ የሉም። መቻል ይህንን አካሄድ መቀየር ይፈልጋል። የራሱ ስታዲየም እንዲኖረው የሚቻለውን ስራ ሁሉ ይሰራል በማለት አፅኖት ሰጥተው ተናግረዋል።


በመጨረሻም ለመርሐግብሩ መሳካት ከፍተኛ አስተዋፆኦ ላደረጉ የሚዲያ አካላት የምስጋና ምስክር ወረቀት ሰጥተዋል።