ጦሩ የወሳኝ ተጫዋቾቹን ውል አራዝሟል

ትናንት እና ዛሬ የነባር ተጫዋቾቹን ውል በማደስ የተጠመደው መቻል በዛሬው ዕለት ወሳኝ ተጫዋቹን በክለቡ ለማቆየት ተስማምቷል።

ማክሰኞ እና ረቡዕ አምስት አዳዲስ ተጫዋቾችን በማስፈረም የዝውውር ገበያውን በይፋ የተቀላቀሉት መቻሎች በትናትናው ዕለት ደግሞ የነባር ተጫዋቾቻቸውን ውል ማደስ ላይ ተጠምደው ከቀትር በፊት አምስት ተጫዋቾችን ለቀጣይ ሁለት ዓመታት በቡድናቸው ለማቆየት ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ተከታታይ ዘገባ አቅርበን ነበር። ዛሬ ደግሞ ሶከር ኢትዮጵያ ባገኘችው መረጃ ወሳኙ የመስመር ተጫዋች ከነዓን ማርክነህ ስድስተኛው ውሉን ያደሰ የቡድኑ ተጫዋች ሆኗል።

ከአዳማ ወጣት ቡድን ተገኝቶ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ አዲስ አበባ ከተማ፣ አዳማ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ አምርቶ የእግርኳስ ህይወቱን የቀጠለው ከነዓን ከሁለት ዓመታት በፊት መቻልን ተቀላቅሎ ድንቅ ግልጋሎት ሲሰጥ የቆየ ሲሆን ውሉ ማለቁን ተከትሎም በክለቡ ለቀጣዮቹ 24 ወራት ዳግም ለመቆየት ስምምነት ላይ ደርሷል።