ስሑል ሽረዎች የነባር ተጫዋቾች ውል አራዘሙ

አስራ አንድ ተጫዋቾች ከስሑል ሽረ ጋር ለመቀጠል ተስማምተዋል።

ቀደም ብለው ወደ ዝውውሩ በመግባት አምስት ተጫዋቾችን ለማስፈረም የተስማሙት ስሑል ሽረዎች አሁን ደግሞ አስራ አንድ ነባር ተጫዋቾችን ለተጨማሪ ሁለት ዓመታት በክለቡ ለማቆየት ውል አራዝመዋል። ከክለቡ ጋር የሚቆዩት ተጫዋቾች ደግሞ ላለፉት ዓመታት በዋናው ቡድን ግልጋሎት የሰጡት ግዙፉ አጥቂ ብሩክ ሐዱሽ፣ ክለቡ ወደ ፕሪምየር ሊጉ ሲያድግ ድርሻ የነበራቸው የመሃል ተከላካዩ ክብሮም ብርሃነ ፣ የቀኝ ተከላካዩ ክፍሎም ገብረሕይወት ፣ ግብ ጠባቂው ዋልታ ዓንደይ ፣ እና አጥቂው ሰይድ ሐሰን ሲሆኑ ክለቡ ከተጠቀሱት ተጫዋቾችም በተጨማሪ ከወዲሁ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ እያሳየ የሚገኘው ተስፈኛው ፀጋይ ፀሐየ፣ ኬቨን አርጉዲ፣ ክብሮም ልዑል፣ አቤል ብርሃነ፣ ሄኖክ ተወልደ እና የቴዎድሮስ ጉዕሽን ውል ለተጨማሪ ዓመታት አራዝሟል።

ቡድናቸውን ለማጠናቀር በእንቅስቃሴ ላይ የሚገኙት ሽረዎች በነገው ዕለትም የተጨማሪ ነባር ተጫዋቾችን ውል ለማራዘም በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛሉ።