ኢትዮ ኤሌክትሪክ አማካይ አስፈርሟል

ከባንክ ጋር የሊጉ ቻምፕዮን የሆነው አማካይ ወደ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ለመቀላቀል ስምምነት ደርሷል።

በአሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ የሚመሩት ኢትዮ ኤሌክትሪኮች ወደ ዝውውሩ በመግባት ተጫዋቾችን በማስፈረም እና ውላቸው የተጠናቀቁትን የነባር ተጫዋቾችን ውል በማረዘም ላይ ይገኛሉ። አሁን ደግሞ አማካይ ሐብታሙ ሸዋለምን በማስፈረም የአንድ ነባር ተጫዋቻቸውን ውል ማራዘማቸውን ክለቡ አሳውቆናል።

የውድድር ዓመቱን በሃያ ሁለት ጨዋታዎች ላይ ተሳትፎ በማድረግ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር የሊጉን ዋንጫ ያነሳው ሐብታሙ በወልድያ ፣ ፋሲል ከነማ፣ አዳማ ከተማ እና ኢትዮጵያ መድን የተጫወተ ሲሆን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ለሁለት ዓመት ለመቆየት ፊርማውን አኑሯል።

ሌላው ከቡድኑ ጋር አብሮ ለመቆየት ውሉን ያራዘመው የቀኝ መስመር ተከላካዩ በጋሻው ክንዴ ሲሆን ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወደ ሊጉ ሲያድግ ትልቅ ድርሻ የነበረው ተጫዋች ነበር።