ድሬዳዋ ከተማ የቅድመ ውድድር ዝግጅቱን ዛሬ ይጀምራል

አሰልጣኝ ይታገሱ እንዳለን የሾሙተረ ብርቱካናማዎቹ በአዳማ ከተማ የቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን ማከናወን ይጀምራሉ።

ባሳለፍነው የውድድር ዘመን በአሰልጣኝ አስራት አባተ ዓመቱን ጀምረው በጊዜያዊ አሰልጣኝ በነበረው ሽመልስ አበበ በ40 ነጥቦች 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠው የቋጩት ድሬዳዋ ከተማዎች ለቀጣዩ የውድድር ዘመን አሰልጣኝ ይታገሱ እንዳለ በአራት ዓመት ኮንትራት ከቀጠሩ በኋላ ዘግየት ቢሉም ወደ ስምንት ወሳኝ ዝውውሮችን መፈፀም ጀምረዋል። ከፕሪምየር ሊጉ አስራት ቶንጆ ፣ አህመድ ረሺድ ፣ መሀመድ ኑርናስር ፣ አብዱሰላም የሱፍ ፣ አቡበከር ሻሚል ፣ መስዑድ መሐመድ ፣ አላዛር መርኔ እና ከከፍተኛ ሊግ ድልአዲስ ገብሬን በማስፈረም የያሬድ ታደሠ ፣ ሔኖክ ሐሰን እና አብዩ ካሳዬን ውል ደግሞ ያራዘሙ ሲሆን ተጨማሪ የአዳዲስ ተጫዋቾችን ዝውውር ከመፈፃማቸው በፊት ወደ ቅድመ ውድድር ዝግጅት ሊገቡ ስለ መሆኑ ክለቡ ለሶከር ኢትዮጵያ አሳውቋል።

የቡድኑ አባላት በዛሬው ዕለት ማክሰኞ በአዳማ ከተማ በሚገኘው ኤክስፕረስ ሆቴል የተሰባሱ ሲሆን ሜዳ ከተገኘ ዛሬ አመሻሹን ካልሆነ ግን ከነገ ነሐሴ 8/2016 ጀምሮ የቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን መከወን ይጀምራሉ።