የአሰልጣኞች አስተያየት | ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 2 –  1 ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ

👉 “በሀገራችን ዋንጫውን እናስቀራለን።” አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው

👉 “ዕድሎች አግኝተን ነበር ግን አልተጠቀምንባቸውም።” አሰልጣኝ አዩብ ካሊፋ

በካፍ የሴቶች ቻምፒየንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣርያ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በመሳይ ተመስገን እና እመቤት አዲሱ ግቦች ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስን 2ለ1 በማሸነፍ ወደ ፍጻሜው የሚያሻግራቸውን ውጤት ካስመዘገቡ በኋላ የሁለቱም ቡድን አሰልጣኞች የሰጡትን አስተያየት እንደሚከተለው አቅርበነዋል።

አሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው – ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ

ስለ ጨዋታው…

“ጨዋታው በጣም ከባድ ነበር፤  ለዋንጫ ስለሆነ ተጫዋቾቼ ላይ በተወሰነ መልኩ ውጥረቶች ይታዩ ነበር። እየመራን ነበር ጎል ተቆጠረብን እንደገና ደግሞ ተጫዋቾቹን ማነሳሳት ነበረብኝ ፤ ባለፈውም ከባድ ጨዋታ ተጫውተናል በ11 ቀናቶች ውስጥ ውጥረት ነበር በተወሰነም መልክ ውጥረቶች ይታዩብናል።”

ከኬኒያ ፓሊስ ጋር በምድብ ጨዋታ ተገናኝተው ለፍፃሜም በተመሳሳይ ስለ መገናኘታቸው…

“ከዚህ በፊት ከኬኒያ ፖሊስ ጋር ደጋግመን ተገናኝተናል በአጠቃላይ ወደ አራት ጨዋታ ተጫውተናል እኛም እነርሱን ሦስት ጨዋታዎችን አሸንፈናቸዋል። ለዋንጫ ከዚህ በፊት ከቪጋ ኩዊንስ ጋር ገጥመን በሀገሩ አስቀርቷል አሁን ደግሞ ዕድለኝነታችን በሀገራችን ዋንጫውን እናስቀራለን ምክንያቱም ጠንካራ ምድብ ነበር ሁለታችንም አሁን የተገናኘነው እና ቡድኔ ዋንጫ ለመብላት ዝግጁ ነው።”

ቡድኑ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ሲደርስ ይቸገራል ፤ ለውጤት ከመጓጓት አኳያ ወይስ ሌላ የተለየ ነገር…

“ለውጤት መጓጓት አንዱ ችግር ነው ፤ ሁለተኛ ደግሞ አብዛኛውን ጊዜ ጨዋታው ትንሽ ጠንከር ስለሚል ወቅቱም የዝናብ ወቅት ስለነበር በተወሰነ እነዚህ ናቸው ችግር ውስጥ እየተከተቱን ያሉት። አሁን ግን ከዛኛው የፍፃሜ ጨዋታ እስከ አሁን አራት ጊዜ ነው ሴካፋ ያዘጋጀው ከአራቱ ዋንጫ የበሉት እንኳን ሦስት ጊዜ ግማሽ ፍፃሜ አልገቡም ዋንጫ ካለማንሳት በስተቀር በማሸነፍም መድረኩ ላይ በመገኘትም ጠንካራ እንቅስቃሴ እያደረግን ነው እና ካለፈው ልምዳችን ተምረን ዋንጫውን የምናነሳበትን መንገድ እንፈጥራለን።”

ስለ አረጋሽ ካልሳ ከነ ጉዳቷ መጫወት…

“ጉዳቱ ሜዳ ላይ የመጣ ነው፤ መጠነኛ ጉዳት እንደሆነ የምናውቀው ነገር አለ።  አረጋሽ በግል የምትፈጥረው ሁለተኛ ደግሞ ቡድኑ ውስጥ በመኖሯ የምትፈጥራቸው ነገሮች አሉ፤ እንደገና ጉዳቱ ሳይደርስባት ቅያሪ አድርገናል። እንግዲህ ቀጣይ ዶክተር አጠገቤ ነው ያለችው የህክምና ሁኔታውን ዐይተን የምንወስነው ይሆናል።”

አሰልጣኝ አዩብ ካሊፋ – ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ

ስለ ጨዋታው…

“ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እንኳን ደስ አላችሁ ማለት እፈልጋለሁ። ጨዋታውን ተቆጣጥረውት ነበር ለዛም ነው ያሸነፉት። ዕድሎች አግኝተን ነበር ግን አልተጠቀምንባቸውም። በርግጥ ዕድለኞችም ነበሩ ግን በመጀመርያው እና በሁለተኛው አጋማሽ የመጨረሻ ደቂቃዎች ብልጫ ነበራቸው ለዛም ነው ግቦች ያስቆጠሩብን።”

ቡድናቸው በውድድሩ ያገኘው አወንታዊ ነገር…

“ጥሩ እግር ኳስ ተጫውተናል፤ ወጣቶች ናቸው ጥሩ ተጫውተዋል። በራስ መተማመናቸውን አጎልብተዋል ፣ እንደ ቡድንም ጥሩ ተንቀሳቅሰዋል በእርግጠኝነት ቀጣይ ከዚህ የተሻለ ሆነው ይቀርባሉ።”

በቀጣይ ስላለባቸው የደረጃ ጨዋታ…

“አሁንም እቅዳችን ጨዋታውን ማሸነፍ ነው፤ ሁልጊዜም እቅዳችን እሱ ነው። ጨዋታውን ለማሸነፍ የተቻለንን እናደርጋለን፤ እናሸንፋለንም።”

ስለ ተጋጣሚያቸው የታክቲክ አቀራረብ ፣ ስለ ውድድሩ እና ስለ ኢትዮጵያ ቆይታቸው…

“ውድድሩ ጥሩ ነበር፤ የተጫዋቾቻችንን አቅም ያየንበት ነው። ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ጋር በተያያዘ በክለብም ሆነ በብሔራዊ ቡድን ደረጃ ተደጋጋሚ ጊዜ ዐይቻቸዋለሁ ዕድሎች ተጠቅመው ጎል ያስቆጥራሉ ‘ታክቲካሊ’ ግን ትንሽ ይቀራቸዋል።”