ሀዋሳ ከተማ የ2017 አምበሎቹን አሳውቋል

የአሰልጣኝ ዘርዓይ ሙሉው ሀዋሳ ከተማ በአዲሱ የውድድር ዘመን ቡድኑን በሜዳ ላይ የሚመሩ ሁለት አምበሎቹን አሳውቋል።

የቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን በክለቡ መቀመጫ ከተማ ሲከውኑ የነበሩት ሀዋሳ ከተማዎች በአሰልጣኝ ዘርዓይ በክረምቱ የዝውውር መስኮት ቢኒያም በላይ ፣ ወንድማገኝ ማዕረግ ፣ ወንድማገኝ ሐይሉ ፣ ዮሴፍ ታረቀኝ ፣ ሰይድ ሀብታሙ ሲያስፈርሙ የእስራኤል እሸቱ ፣ ምንተስኖት ጊምቦ ፣ ሠለሞን ወዴሳ እና ዳዊት ታደሠን ውል ደግሞ በማራዘም በትላንትናው ዕለት ወደ ድሬዳዋ አምርተዋል።


ቡድኑም ለ2017 የሚጠቀማቸውን ሁለት አምበሎች ሲታወቁ በዚህም ድሬዳዋ ከተማን በመልቀቅ ላለፉት ሁለት ዓመታት ሀዋሳ ከተማን የተቀላቀለው እና የ2016 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሁለተኛው ዙር ላይ ተጨማሪ የሁለት ዓመት ውል የፈረመው የመሐል ተከላካዩ በረከት ሳሙኤል የቡድኑ የመጀመሪያ አምበል ሲሆን በኢትዮጵያ መድን እና ባህርዳር ከተማ ግልጋሎት ከሠጠ በኋላ ወደ ልጅነት ክለቡ ተመልሶ በመጫወት ላይ የሚገኘው ሌላኛው ተከላካይ ሠለሞን ወዴሳ ሌላኛው የቡድኑ አምበል ሆኗል።