የሊግ ካምፓኒው ውሳኔ ታውቋል

የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አወዳዳሪ አካል ወልቂጤ ከተማን በተመለከት ውሳኔ አስተላለፈ።

የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አወዳዳሪ አካል የሆነው የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አክስዮን ማኅበር ዛሬ ባደረገው ስብስባ ከዳኞች፣ ከጨዋታ ታዛቢዎች እና ሌሎች አካላት የቀረቡለትን ሪፖርት መሰረት አድርጎ  የዲሲፕሊን ውሳኔዎችን ይፋ አድርጓል። ይህንን ተከትሎ በሁለቱም የጨዋታ ሳምንታት አነጋጋሪ የነበረው የወልቂጤ ከተማ ጉዳይ ላይ ውሳኔ አስተላልፏል። አወዳዳሪው አካል ሠራተኞቹ በአንድ የውድድር ዓመት በሁለት ጨዋታዎች በፎርፌ መሸነፋቸውን ጠቅሶ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የዲስፕሊን መመርያ ክፍል 3፣ አንቀፅ 69፣ በንኡስ አንቀፅ 3፣ ተራ ቁጥር 14 መሰረት ከ2017 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ መሰረዛቸውን ይፋ አድርጓል።

የሊግ ካምፓኒው አያይዞም በሁለቱም የጨዋታ ሳምንታት ወልቂጤ ከተማን በፎርፌ ያሸነፉት የመቻል ስፖርት ክለብ እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ስፖርት ክለብ ውጤት እንዳይመዘገብ ውሳኔ አስተላልፏል።