ከፍተኛ ሊግ | ጋሞ ጨንቻ አምስት አዳዲስ ተጫዋቾችን አስፈርሟል

በአሰልጣኝ ማቲያስ ለማ የሚመሩት ጋሞ ጨንቻዎች አዳዲስ ተጫዋቾችን ሲያስፈርሙ የሰባት ነባሮችንም ውል አድሰዋል።

በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ላይ ጠንካራ ተፎካካሪ ከሆኑ ክለቦች መካከል አንዱ የሆነው ጋሞ ጨንቻ ለዘንድሮው የሊጉ ተሳትፎው ጠንካራ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመገኘት በአሰልጣኝ ማቲዮስ ለማ እየተመራ ወደ ዝግጅት የገባ ሲሆን ቡድኑም አምስት አዳዲስ ተጫዋቾችን ሲያስፈርም የሰባት ነባሮችን ውል ደግሞ አድሷል።

ቡድኑ ካስፈረማቸው ተጫዋቾች መካከል በአርባምንጭ ከተማ ረዘም ላሉ ዓመታት በቀኝ ተከላካይነት እና አምበልነት ያገለገለው ወርቅይታደስ አበበ ፣ በተመሳሳይ በአርባምንጭ እንዲሁም በጋሞ ጨንቻ ቆይታ የነበረው የመሐል ተከላካዩ አንድነት አዳነ ፣ ከአርባምንጭ ወጣት ቡድን እስከ ዋናው የተጫወተው የግብ ዘቡ መኮንን መርዶክዮስን ጨምሮ ፣ ተከላካዩን ዘካሪያስ ጀብሮን ከቦዲቲ ከተማ እና አጥቂው ቢኒያም ከበደ ከብር ሞሌ ከተሰኘው ቡድን የተቀላቀሉ ተጫዋቾች ሆነዋል።

ከአዳዲስ ፈራሚዎች በተጨማሪ ክለቡ የአቦነ ገነቱ ፣ ፋሲል ፋንታሁን ፣ ንጋቱ ፀጋዬ ፣ ማቴዎስ ኤልያስ ፣ አሸናፊ ሀይለማሪያም ፣ በለጠ በቀለ እና ምትኩ ባንዳ የተባሉ ተጫዋቾችን ውል ለተጨማሪ ዓመት አራዝሞላቸዋል።