የኢትዮጵያ እና ኤርትራ ጨዋታዎች የሚደረግበት ስፍራ ታወቀ

በቻን የማጣሪያ ውድድር የተገናኙት ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ከሜዳቸው ውጪ የሚያደርጓቸው የደርሶ መልስ ጨዋታዎች የት እንደሚደረጉ ተረጋግጧል።

በምስራቅ አፍሪካ ሦስት ሀገራት በሚዘጋጀው የ2025 የቻን ውድድር ላይ ለመሳተፍ በየቀጠናው የማጣሪያ መርሐ-ግብሮች መደረግ የሚጀምሩ ሲሆን ሀገራችን ኢትዮጵያም ከጎረቤት ሀገር ኤርትራ ጋር ወሳኝ ጨዋታ ለማድረግ ቀጠሮ ተይዞላታል።

ሁለቱም ሀገራት በሜዳቸው ለመጫወት ፍቃድ ያለው ስታዲየም የሌላቸው በመሆኑ የደርሶ መልስ መርሐ-ግብሩ የት ሊከናወን ይችላል የሚለው ሲጠበቅ የነበረ ሲሆን በትናንትናው ዕለት ባቀረብነው ዘገባ ኢትዮጵያ አዲስ አበባ ስታዲየምን ኤርትራ ደግሞ ታንዛኒያ አዛም ኮምፕሌክስ ስታዲየምን ለመጠቀም መጠየቃቸውን አስነብበናል። አሁን የዝግጅት ክፍላችን ባደረገችው ማጣራት የሁለቱም የደርሶ መልስ ጨዋታ በደቡብ ሱዳን ጁባ ስታዲየም እንደሚደረግ ተመልክቷል።

ከመርሐ-ግብሩ ቀን ጋር በተያያዘ ሽግሽጎች ሊደረጉ እንደሚችል የሰማን ሲሆን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንም ከአሠልጣኙ ጋር እንዲሁም ከዝግጅት ጋር ተያይዞ ያለውን ጉዳይ ዛሬ አልያም ነገ ይፋ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል።