ቅዱስ ጊዮርጊስ ተስተካካይ ጨዋታውን በድል ተወጣ

ቅዱስ ጊዮርጊስ በብሄራዊ ቡድን ምክንያት ወደ ሌላ ጊዜያት ላለፉት 3 የሊግ ጨዋታዎች አንዱን ዛሬ አሰላ ላይ አድርጎ 4-1 አሸንፎ ተመልሷል፡፡

የጨዋታው አንደኛ አጋማሽ ሊጠናቀቅ 8 ደቂቃዎች ያህል እስኪቀሩ ድረስ 0-0 የነበረው ጨዋታ በቅፅበት ተቀይሮ ዘንድሮ በድንቅ አቋም ላይ የሚገኘው ኡመድ ኡኩሪ በ5 ደቂቃዎች ውስጥ ሁለት ግቦች ከመረብ ሲያሳርፍ የመስመር አማካዩ በሃይሉ አሰፋ ተጨማሪዋን ግብ አስቆጥሮ የመጀመርያው አጋማሽ ተጠናቋል፡፡

ከእረፍት መልስ ሙገር 1 ግብ አስቆጥሮ የግብ ልዩነቱን ቢያጠብም በ86ኛው ደቂቃ ላይ ፍፁም ገብረማርያም በቀድሞ ክለቡ ላይ ባስቆጠረው የፍፁም ቅጣት ምት ግብ ጨዋታው 4-1 ተጠናቋል፡፡

በጨዋታው አዳነ ግርማ በጉዳት ተቀይሮ የወጣ ሲሆን የቀኝ መስመር ተከላካዩ አሉላ ግርማ አብዛኛውን የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ቅዱስ ጊዮርጊስን በአምበልነት መርቷል፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስ በተስተካካይ ጨዋታ ያገኘውን ድል ተጠቅሞ በ8 ጨዋታ ሙሉ 24 ነጥቦች የሰበሰበ ሲሆን 9 ጨዋታ ካደረገው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያለውን የነጥብ ልዩነት ከወዲሁ 6 ነጥብ የደረሰ ሲሆን የከፍተኛ ግብ አግቢነቱን ኡመድ ኡኩሪ በ9 ግቦች ይመራል፡፡

{jcomments on}