የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ባለፈው ሰኞ ፖርቱጋላዊው ማርያኖ ባሬቶ አዲሱ የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ እንዲሆኑ መወሰናቸውን ቢያሳውቁም አሁንም አሰልጣኝ ሆኖ የተመረጠው ሰው ማንነት እና የምርጫው ሂደት ግራ አጋቢ ሆኗል፡፡
ፌዴሬሽኑ የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ፌዴሬሽኑ አሰልጣኝ ማርያኖን አሰልጣኝ አድርጎ ለመሾም የወሰነው በቀዳሚ እጩነት ከተያዙት ጎራን ስቴፋኖቪች ጋር የነበረው የስልክ ግንኙነት በመቋረጡ እንደሆነ እየተነገረ ነው፡፡ አሁን ደግሞ ከአሰልጣኙ ጋር የተቋረጠው ግንኙነት መስመር በመያዙ ከሰርቢያዊው ጋር በድጋሚ የደሞዝ ድርድር ውስጥ እንደገቡ እየተነገረ ነው፡፡
አሰልጣኙ የሚያቀርቡት የደሞዝ እና የጥቅማ ጥቅም ጥያቄ በፌዴሬሽኑ ተቀባይነት ካገኘ የቀድሞው የጋና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ጎራን ስቴፋኖቪች ተሸመዋል የተባሉት ማርዮ ባሬቶን በልጠው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ መሆናቸው እርግጥ ይሆናል፡፡
የፌዴሬሽኑ ሰዎች ይህን ይበሉ እንጂ ከባሬቶ የቅጥር ውሳኔ በኋላ በአሰልጣኙ ብቃት እና የቀድሞ ታሪክ ላይ ጥያቄ በማንሳት ከሚድያው እና ደጋፊዎች የቀረበበት ትችት እና ተቃውሞ ውሳኔውን እንዳስቀየረው በበርካቶች ታምኖበታል፡፡
{jcomments on}