በ መሸሻ ወልዴ
የኢትዮጵያ የሴቶች ብሄራዊ ቡድን በናሚቢያ ለሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ግንቦት 17 ቀን ወሳኙን የማጣሪያ ጨዋታ ከጋና ብሄራዊ ቡድን ጋር የሚያካሄድ ሲሆን ለእዚህም ፍልሚያ ይረዳው ዘንድ የአቋም መለኪያ ጨዋታዎቹን በማከናወን ላይ ይገኛል፡፡ ሉሲዎቹ የመጀመሪያ የወዳጅነት ጨዋታቸውን ከናሚቢያ በቪክቶሪያ ከተማ ላይ አድርገው 1ለ0 የተሸነፉ ሲሆን ዛሬ እሁድ ደግሞ በአዲስ አበባ ስታዲየም በውጤት ደረጃ ጠንካራ ከሆነው የካሜሩን አቻቸው ጋር ተጫውተው 0ለ0 ሊለያዩ ችለዋል፡፡ የዛሬው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በእንቅስቃሴም ሆነ በተደጋጋሚ ወደ ግብ በመጠጋትና ሙከራዎችን በማድረጉ ረገድ ደከም ያሉ ስለነበሩ ተመልካቹ በጨዋታው ሳይረካ ከሜዳ ወጥቷል፡፡ የሉሲዎቹ ስብስብ በጨዋታው የመጀመሪያ ክፍለ ጊዜ ኳስን ለጓደኛ በትክክል ለማቀበልና ተረጋግተውና እርስ በእርስም ተናበው ለመጫወት ያደረጉት ጥረት አናሳ በመሆኑ፣ ኳስ ለመቀበልም ብቅ ከማለት ይልቅ ኳሱ የቆሙበት ቦታ ድረስ እስኪመጣላቸውም የሚጠብቁ በመሆኑ እንዲሁም ረጃጅምና ግዙፍ የሆኑት የካሜሩን ተጨዋቾችን በምን መልኩ ሊበልጧቸው እንደሚችሉ አህምሮአቸውን ፈጣን አድርገው ውሳኔ ስላልወሰኑ በዕለቱ ጥሩ የሚባል እንቅስቃሴ እንዳያደርጉ አስችሎአቸዋል፡፡
ሉሲዎቹ የሁለተኛው አጋማሽ ላይ ቱቱ በላይ ሰናይት ቦጋለን ቀይራ ከገባች በኃላ በንፅፅር ከመጀመሪያው አጋማሽ በተሻለ የእንቅስቃሴ የተወሰነ ለውጥ ለመታየት ቢችልም በ79ኛው ደቂቃ ላይ ቱቱ በላይ በእግሯ ላይ በደረሰባት ጉዳት በቃሬዛ ከሜዳ ልትወጣና ለህክምናም ወደ ቤተዛታ ሆስፒታልም ልታመራ ችላለች፡፡ የሉሲዎቹ አማካይ ቱቱ በላይ በእግሯ ላይ በጨዋታው የደረሰባት ጉዳት በካሜሩን ተጨዋች ተረግጣ እግሯ ላይ ቅጥቅጥ ስለደረሰባት ሲሆን ራጅ ከተነሳች በኋላም ሕክምናዋን እያከናወነች ይገኛል፤ የሉሲዎቹን አማካይ አስመልክቶ እንደ ህክምና ባለሙያዎቹ እምነት ከሆነ ከጉዳቱ ለመዳን አጭር ቀናቶች እንጂ ረጅም ያለ ጊዜም እንደማይወስድባትም እየተናገሩም ይገኛሉ፤ ቱቱ በላይ በመጎዳቷ ሳቢያ ዳሽን ቢራ በእዚህ ሳምንት መጨረሻ ከቅድስተ ማሪያም ጋር ጎንደር ላይ የሚያደርገው የፕሪምየር ሊግ ጨዋታ ያመልጣታል፡፡
የዛሬውን የሉሲዎቹንና የካሜሩንን ግጥሚያ በማስመልከት የካሜሩኑ አሰልጣኝ የወዳጅነት ጨዋታውን ማድረጋቸው አቋማቸውን በመፈተሸ ረገድ ጥሩ ትምህርት እንደሰጣቸው በመግለፅ ከኢትዮጵያ ቡድን ተጨዋቾች መሃል ቀደም ሲልም ያውቋት የነበረውን ተከላካይዋን ብዙሀን እንዳለን ሊያደንቅዋት ችለዋል፡፡ የሉሲዎቹ ተከላካይ በእርግጥም በዕለቱ ኳስን በተረጋጋ ሁኔታ ይዛ በመጫወት ለጓደኞቿም በትክክል ማቀበልና የካሜሩንተረጋግታ በመጫወት ጥሩ ስትንቀሳቀስ ያየናት ሲሆን እንቅስቃሴዋም የቀድሞ ጥሩ ብቃቷን ከረጅም ጊዜ በኋላ ዳግም እንድንመለከትላት ያሳየን ሆኗል፡፡
{jcomments on}