የውድድር ዘመኑ መጠናቀቅን ተከትሎ የተጫዋቾች ዝውውር በክረምቱ ይጠበቃል፡፡ ከተለያዩ ክለቦች ጋር የተያያዙ የዝውውር ጭምጭምታዎችን፣ የኮንትራት ማራዘሚያ ስምምነቶችን እና መጠናቀቃቸው የተነገረላቸው ዝውውሮች ከዚህ በመቀጠል ተዳሰዋል፡፡ (የሁሉም ዜናዎች ምንጭ ዛሚ-ስፖርት ብሄራዊ ነው )
– ደደቢት የነባር ተጫዋቾቹን ኮንትራት ማራዘሙ ተነግሯል፡፡ ሰማያዊው ጦር ለቀጣዩ አመት ተጠናክሮ ለመቅረብ በተጫዋቾች ዝውውር እና ኮንራት ማራዘም እንደሚጠመድም እየተነገረ ነው፡፡ ደደቢት ኮንትራታቸውን ካራዘመላቸው 6 ተጫዋቾች መካከልም ግብ ጠባቂው ታሪክ ጌትነት ፣ ተከላካዩ አዳሙ መሃመድ እና ተስፈኛው ሄኖክ ኢሳያስ ይገኙበታል፡፡
– ዳሽን ቢራ ከኢትዮጰያ ቡና ጋር የተለያየው ፋሲካ አስፋውን ለማስፈረም ፍላጎት አሳይቷል፡፡
– ዳዊት ፍቃዱ ከደደቢት ጋር የመቀጠሉ ነገር በዚህ ሳምንት ይለይለታል፡፡ ዘንድሮ መልካም የውድድር ዘመን ያሳለፈው ዳዊት ስሙ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር የተያያዘ ሲሆን በደደቢት ኮንትራት እንደተራዘመለትም እየተወራ ነው፡፡
– የመብራት ኃይሉ በረከት ይስሃቅ በቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት ይፈለጋል፡፡ አጥቂው በመብራት ኃይል ኮንትራቱን ጨርሷል፡፡
– ደደቢት የቅዱስ ጊዮርጊሱን ሁለገብ ተጫዋች ያሬድ ዝናቡ ለማስፈረም ጥረት ጀምሯል፡፡ ያሬድ በቅዱስ ጊዮርጊስ ዘንድሮ ብዙ ተሳትፎ አላደረገም፡፡
– ቢያድግልኝ ኤልያስ እና ፍፁም ገብረ ማርያም ለሙከራ ወደ ደቡብ አፍሪካ ተጉዘዋል፡፡ ቢያድግልኝ ወደ ግብፅ ሊያመራ እንደሚችልም ተወርቷል፡፡
– ኢትዮጵያ ቡና የቀድሞ ተጫዋቹ ወሰኑ ማዜን እና አማካዩ ኤልያስ ማሞን ለማስፈረም እየጣረ ነው፡፡ ወሰኑ በ1990ዎቹ መጨረሻ እና 2000 መጀመርያ ለኢትዮጵያ ቡና ተጫውቷል፡፡
– ዳሽን ቢራ ተጨማሪ አጥቂ እና አማካዮች ለማስፈረም እንቅስቃሴ ማድረግ ጀምሯል፡፡ የጎንደሩ ክለብ ፊሊፕ ዳውዚ ፣ መሀመድ ናስር ፣ ኤልያስ ማሞ እና ያሬድ ዝናቡን በዝውውር ራዳሩ አስገብቷል፡፡
– ደደቢት የቅዱስ ጊዮርጊሱ ፍፁም ገብረ ማርያምን ማስፈረም ይፈልጋል፡፡
– ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የመከላከያው የአጥቂ አማካይ ፍሬው ሰለሞንን ማስፈረሙ ተወርቷል፡፡ ባንክ ለዝውውሩ 850ሺህ ብር ወጪ እንዳደረገ ተነግሯል፡፡
– ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከፍሬው ዝውውር በተጨማሪ የማጥቃት ባህርይ ባላቸው አማካዮች ዝውውር ላይ አነጣጥሯል፡፡ የኢትዮጵያ ቡናዎቹ ሰለሞን ገብረመድህን እና ኤፍሬም አሻሞ ፣ የመብራት ኃይሉ አብዱልከሪም ሃሰን እንዲሁም ፋሲካ አስፋው በባንክ ራዳር ውስጥ የገቡ ተጫዋቾች ናቸው፡፡