አታላንታ ትውልደ ኢትዮጵያዊውን ተጫዋች ከባርሴሎና አስፈረመ

ባለክህሎቱ የመስመር ተጫዋች አንዋር ሜዴይሮ የባርሴሎና ወጣት ቡድንን ለቆ ወደ ጣልያኑ አታላንታ አምርቷል።

ላለፉት ዓመታት በባርሰሎና ሁለተኛ ቡድን ቆይታ የነበረው የ18 ዓመቱ ትውልደ ኢትዮጵያዊ አንዋር መዴይሮ ወደ ጣልያኑ አታላንታ መፈረሙ ታማኙ ጣልያናዊ ጋዜጠኛ ፋብሪዝዮ ሮማኖ ገልጿል። በመስመር እና በአጥቂነት መጫወት የሚችለው አንዋር በአታላንታ በቅርቡ ከሁለተኛው ቡድን ያድጋል ተብሎ ከሚጠበቀው ሌላው ትውልደ ኢትዮጵያዊ እዮብ ዛምባታሮ ጋር የሚገናኝ ይሆናል።

በአውሮፓውያን አቆጣጠር በ2002 አዲስ አበባ የተወለደውና በስፔናውያን ቤተሰቦች በማደጎነት ወደ ስፔኗ ጋላሲያን ግዛት ገና በጨቅላነቱ ያመራው አንዋር ሜዴይሮ ሮድሪጌዝ በሴሎታ ቪጎ ህፃናት ቡድን አድጎ በ2015 ነበር ወደ ዝነኛው የባርሴሎና አካዳሚ ላማሲያ ያመራው። በወቅቱ በዝውውሩ ምክንያት ባርሳዎች ከሴልታ ቪጎ ጋር ከፍተኛ ውዝግብ ውስጥ ገብተው የነበረ ሲሆን በየዓመቱ ባሳየው እድገት ባለፈው የውድድር ዓመት ከ19 ዓመት በታች ቡድን (ጁቬኔይል ቢ) መቀላቀል ችሎ ነበር።

ለተጫዋቾች እድገት ተመራጭ እየሆነ የመጣው የወቅቱ የአውሮፓ ክስተት ቡድን አታላንታ ቤርጋሞ ትውልደ ኢትዮጵያዊውን ባለ ክህሎት ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋግረዋል ተብሎ ይጠበቃል።

ከዚህ ቀደም ሶከር ኢትዮጵያ ስለ አንዋር ያቀረበቻቸው ዘገባዎች፡-

1. LINK

2. LINK

👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!


© ሶከር ኢትዮጵያ